ዶላር ከገበያ መጥፋቱን ነጋዴዎች ይናገራሉ

ጥር ፳፰ (ሀያ ስምንት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ኢትዮጵያ አምና የግብርና ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ ያገኘችው የውጭ ምንዛሬ አነስተኛ መሆን መንግስት ከሚከተለው ፖሊሲ ጋር ተደማምሮ የዶላር እጥረት እንዲፈጠር ማድረጉን ነጋዴዎች ይናገራሉ። በተለያዩ የአስመጪነት ስራ ላይ የተሰማሩ ነጋዴዎች ዶላር በበቂ ሁኔታ ለማግኘት ባለመቻላቸው፣ የንግድ እንቅስቃሴያቸው ተዳክሟል።

ዶላር ለማግኘት ኤልሲ ከፍተው ወረፋ መጠበቅ ከጀመሩ 5 ወራቸው መሆኑን ካፒታል ያነጋገራቸው የተለያዩ የኢንዱስትሪ ሃለፊዎች ገልጸዋል።

አንዳንድ ድርጅቶች ጥሬ እቃዎችን ከውጭ ለማስገባት ባለመቻላቸው ምርታቸውን ለመቀነስ ተገደዋል። በዚህ ከቀጠለም አንዳንዶች ድርጅቶቻቸውን ሊዘጉ እንደሚችሉ አስጠንቅቀዋል።

መንግስት የዶላር እጥረት የለም በማለት ቢከራከርም፣ ነጋዴዎች ግን የሚቀበሉት አልሆነም። ምንም እንኳ ከአጠቃላይ የንግድ እንቅስቃሴው መዳከም ጋር ተያያዞ፣ በእቃዎች ላይ አጠቃላይ የዋጋ ጭማሪ ባይታይም፣ የንግድ እንቅስቃሴው ሞቅ በሚልበት ጊዜ የሚፈጠረው የዋጋ ጭማሪ ከፍተኛ ሊሆን እንደሚችል ባለሙያዎች እንደሚያስጠነቅቁ ጋዜጣው ዘግቧል።

በአገሪቱ ውስጥ የሚታየው የዶላር እጥረት መንስኤው ከምርት እጥረት ጋር የተያያዘ ብቻ ሳይሆን ፣ በሙስና ምክንያት ወደ ውጭ የሚወጣው ገንዘብ በመበራከቱ ነው።

ኢሳት ባለፈው ሳምንት በአገሪቱ የውጭ ምንዛሬ እጥረት መከሰቱን መዘገቡ ይታወሳል።