ከፍተኛው ፍርድ ቤት የእግድ ትእዛዝ የሰጠበት የኢቲቪ ፊልም ቀረበ

ጥር ፳፰ (ሀያ ስምንት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት አራተኛ ወንጀል ችሎት ኢቲቪ ጂሀዳዊ ሀረካት በሚል ርእስ ሊያስተላለፍ የነበረውን ፊልም እንዳይተላለፍ ቢያግድም፣ እግዱ በሰአታት ውስጥ ታጥፎ ፊልሙ በኢቲቪ ተላልፎአል።

ኢሳት ውሳኔው እንደተላለፈ የሙስሊም መሪዎች ጠበቃ የሆኑትን አቶ ተማም አባቡልጋን አነጋግሮ ፍርድ ቤቱ  የእግድ ትእዛዝ  ውሳኔ ማስተላለፉን ለማረጋጥ ችሎ ነበር ።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ኢቲቪ ያስተላለፈውን ውሳኔ በመቃወም በመላ አገሪቱ የኤስ ኤም ኤስ መልእክቶች ተሰራጭተዋል። መልእክቱ ” ይድረስ ለሁሉም” የሚል ርእስ ያለው ሲሆን ” ነገ ማክሰኞ በሚተላለፈው ፍጹም በውሸት የተቀነባበረ የኢቲቪ ድራማ ሙስሊሙን እና ክርስቲያኑን ለማጋጨት ስለሆነ እንጠንቀቅ፣ መልክቱን ለ10 ሰዎች ያድርሱ” የሚል መሆኑን የኢሳት የአዲስ አበባ ዘጋቢ ገልጿል።

በዚሁ ዙሪያ ላይ አስተያየታቸውን የሰጡ በርካታ ኢትዮጵያውያን መንግስት ክርስቲያኑንና ሙስሊሙን በማጣላት ከእጁ እያፈተለከ የመጣውን ህዝባዊ ድጋፍ መልሶ ለማግኘት ሙከራ ማድረጉን ገልጸዋል። አቶ ኡመር የተባሉ ሙስሊም ኢትዮጵያዊ የመንግስትን ድርጊት አውግዘው፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ጨዋና አዋቂ በመሆኑ በመንግስት ፕሮፓጋንዳ ተታልሎ ለግጭት አይነሳም ብለዋል።

“የኢትዮጵያ ህዝብ ከዳር እሰከዳር መንግስት እንደሌለው ተገንዝቧል” የሚሉት አቶ ኡመር “የመንግስት ድርጊት በሁሉም ላይ ተራ በተራ እንደሚደርስ አስጠንቅቀዋል

በደሴ ከተማ ነዋሪ የሆነው ሙስሊም ወጣት በበኩሉ ኢቲቪ የሰራውን ድራማ እንኳን ሙስሊሙ ክርስቲያኑም አይቀበለውም ብለዋል

መንግስት እየወሰደ ያለው እርምጃ የኢትዮጵያን ህልውና አደጋ ላይ የሚጥል መሆኑንም ወጣቱ በአጽንኦት ተናግሯል

በሌላ በኩል ደግሞ በስዊዘርላንድ የሚኖረው ሞጎላ መንግስት ሰዎችን ለመወንጀል ሲፈልግ እንዲህ አይነት ዘዴ እንደሚጠቀም ጠቁሞ፣ መንግስት ለ20 አመታት ሲጠቀምበት የነበረውን ዘዴ መለወጥ አልቻለም ብሎአል።

በክርስቲያን እና ሙስሊሙ ማካከል ለረጅም ጊዜ የቆየ ትስስር እንዳለ የገለጠው ሞጎላ፣ ሙስሊሞች ጀሀድ ሊያውጁ ነው ተብሎ የቀረበው እንዳሳዘነው ገልጿል

ኢቲቪ ያቀረበው ፊልም የሙስሊም መሪዎችን ከአልሸባብ እና ከአልቃይዳ ጋር አያይዞ የሚወነጅል ነው። ኢህአዴግ ላለፉት 20 አመታት ተመሳሳይ ድራማዎችን እየሰራ ለስልጣኔ ያሰጉኛል የሚላቸውን ሁሉ ለማጥፋት ያደረገውን ሙከራ የሚያስታውሱ ሰዎች፣ ይህም ፊልም ሙስሊሙንና ክርስቲያኑን ለማጋጨት አይችልም በማለት አስተያየታቸውን ለኢሳት የሰጡ በርካቶች ናቸው።

የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዶ/ር ሽፈራው ተክለማርያም ትናንት የሀይማኖት መሪዎችን ሰብስበው ፣ ከወራት ጥረት በሁዋላ አሁንም በህዝቡ ውስጥ ያለውን ግራ መጋባት ለመቅረፍ እንዳልተቻለ ገልጸዋል። የሚንስትሩ ንግግር መንግስት ህዝቡን በተለይም ክርስቲያኑን ከሙስሊም ጋር ለማጋጨት ያደረገው ቅስቀሳ አለመሳካቱን የሚያሳይ ነው በማለት ዘጋቢያችን ገልጿል።