የኢትዮጵያ የድንበር ኮሚቴ ከሱዳን ጋር ያለውን ድንበር ለማካለል የሚደረገውን እንቅስቃሴ አወገዘ

ኀዳር ፳፪ (ሃያ ሁለት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በህወሃት የሚመራው የኢትዮጵያ መንግስት ተወካዮች የኢትዮጵያን ሕዝብ ሳያማክሩና ታሪካዊ ተግዳሮቶችን ከግምት ሳያስገቡ ለዘመናት በኢትዮጵያ ስር የነበሩትን ድንበሮች ለሱዳን አሳልፈው ለመስጠት የሚያደርጉትን ሚስጥራዊ ድርድሮች በአፋጣኝ አቁመው ሕጋዊን መንገድ እንዲከተሉ ማሳሰቢያቸውን ሰጥተዋል።
ቁጥራቸው 25 የሚሆኑት የሲቪክና የፖለቲካ ማህበራት በጋራ ያቋሙት የኢትዮጵያ የድንበር ኮሚቴ፣ የአገሪቱ ሉአላዊ ህልውና ለ አደጋ የሚያጋልጡና ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት በቀጣናው እንዳይኖር ሊያደርግ የሚችለውን የእንግሊዝ የ19ኛው ክፍለዘመን የቅኝ ግዛት የድንበር ውል ኢትዮጵያ ልትዳኝ እንደማይገባትና ይህንንም አስመልክተው ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሃፊ ባንኪ ሙንና ለአፍሪካ ሕብረት በደብዳቤ አቤቱታቸውን አስገብተዋል።ዓለምአቀፉ ማኅበረሰብ ጉዳዩን በአንክሮ ማየት እንደሚገባውና በአናሳዎች የሚመራው የህወሃት መራሹ መንግስት ሕዝባዊ መሰረት እንደሌለው እንዲያውቁት የግንዛቤ ማስጨበጥ ስራዎችን እየሰሩ ነው። ማኅበሩ ባወጣቸው 5 የአቋም መግለጫዎቹ የኢትዮጵያን ሉአላዊ ድንበር ለማስከበር የመከላከያ ሰራዊቱ ከሕዝቡ ጋር እንዲቆም ጥሪ አቅርበዋል።
ለተባበሩት መንግስታት፣ለአፍሪካኅብረት፣ለሰብዓዊ መብት ተሟጓች ድርጅቶች ሁኔታውን በኢሜል፣በፋክስ፣በተለያዩ መገናኛ ብዙሃን ዜጎች እንዲያሳውቁም ጠይቀዋል።የመገናኛ ብዙሃን የአገር ክዳቱን በመረጃ በማስደገፍ ለሕዝቡ በወቅቱ እንዲያሳውቁ፣ የአገሪቱ ምሁራን ውይይት ያልታከለበትናለሕዝብ ለውይይት ሳይቀርብ በፓርላማ መጽደቅ እንደሌለበት ግፊት እንዲያደረጉም አሳስቧል።
በመጨረሻም ሁሉም ኢትዮጵያዊ የአገር ክህደቱን በማውገዝ በቅርቡ በሚጠሩት የተቃውሞ ሰልፎች ላይ እንዲሳተፍ ጥሪውን አቅርቧል።