የባለስልጣናት ጣልቃ ገብነት የጋዜጠኞችንና የሚዲያ ነፃነትን ገፏል ሲሉ ጋዜጠኞች ተናገሩ

ጥር ፳፮ (ሃያ ስድት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በሚኒስትሮች በሚመራው የጋዜጠኞች ስልጠና ላይ የኢህአዴግ ባለስልጣናት ጣልቃ ገብነት የጋዜጠኞችን እና የሚዲያውን ነፃነት የገፈፈ መሆኑን የስልጠናው ተሳታፊ የሆኑ ጋዜጠኞች ተናገሩ፡፡ ባህርዳር ከተማ በማካሄድ ላይ ባለው በዚህ የጋዜጠኞች ስልጠና ላይ ” የፕሬስ ነፃነት በሀገሪቱ ሊኖር ባለመቻሉ የመንግስት መገናኛ ብዙሀን ድርጅት ጋዜጠኞች ሳይቀር ተሸማቀው እንዲሰሩ እየተደረገ ያለው የአስራር ስርዓት እስከ መቼ ፍፃሜ ያገኛል?” ብለው ላነሱት ጥያቄ “የሚዲያ አመራሮች ችግር እንጂ የእኛ ችግር አይደለም” ሲሉ የብአዴን ጽ/ቤት ሐላፊና ም/ል ፕሬዚዳንቱ እንዲሁም የአማራ ብዙሀን መገናኛ ድርጅት የቦርድ ሊቀመንበር አቶ አለምነው መኮነን መልስ ሰጠዋል፡፡

የአማራ ብዙሃን መገናኛ ድርጅት ጋዜጠኞች በገጠማቸው ፖለቲካዊ ጫናና ነፃነት እጦት ሳቢያ  በርካታ ጋዜጠኞች ድርጅቱን የለቀቁ ሲሆን ስርዓቱ አላንቀሳቅስ ያላቸው በርካታ ጋዜጠኞች ወደፊትም ለመልቀቅ በማመቻቸት ላይ መሆናቸው ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ ጋዜጠኞች ተናግረዋል፡፡

ከጥር 12 ጀምሮ በመካሄድ ላይ ባለው በዚህ ስልጠና ላይ የንግድና ኢንዱስትሪ ፣የግብርናና ገጠር ልማት፣የውጭ ጉዳይና ሀገር ውስጥ ደህንነት ፖሊሲና ስትራቴጂዎች ዋና አጀንዳዎች መሆናቸውም ታውቋል፡፡