የሃይማኖት ተቋማት ለብአዴን ጽህፈት ቤት ማሰሪያ ገንዘብ እንዲያዋጡ ታዘዙ

ግንቦት ፳፩(ሃያ አንድ)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በቀወት ወረዳ በሸዋ ሮቢት ከተማ ለሚገነባው የብአዴን ጽህፈት ቤት ማሰሪያ በወረዳዋ የሚገኙ ቤተክርስቲያኖች በነፍስ ወከፍ  1 ሺ 500 ብር እንዲከፍሉ በመታዘዛቸው፣ አስተዳዳሪዎቹ ገቢ ማድረጋቸውን ለኢሳት ገልጸዋል።

የሃይማኖት ተቋማት ከፖለቲካ ጣልቃ ገብነት ነጻ እንደሆኑ ህግ ቢደነግግም፣ በተግባር የምናየው የዚህን ተቃራኒ ነው ያሉት ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ አስተዳዳሪዎች፣ ገንዘቡን ለጽህፈት ቤቱ ወስደው ያስረከቡት ከመንግስት የሚመጣውን በቀል በመፍራት መሆኑን ተናግረዋል።

በከተማዋ የሚኖሩ ሰራተኞችም እንዲሁ ያለፍላጎታቸው ገንዘብ እንዲያዋጡ መገደዳቸውን አንዳንድ ሰራተኖች ገልጸዋል።

ከዚህ ጋር በተያያዘ በክልሉ የሚኖሩ ተወላጆች ለመለስ ፋውንዴሽን ማሰሪያ በሚል በነፍስ ወከፍ 50 ብር እንዲከፍሉ እየተደረገ ነው። የከተማ ነዋሪዎች እና አርሶ አደሮች ግብር ለመክፈል በሚቀርቡበት ወቅት ለመለስ ፋውንዴሽን ማሰሪያ ተጨማሪ ገንዘብ የሚጠየቁ ሲሆን፣ ለመክፈል ፈቃደኛ ያልሆኑት አርሶ አደሮች ችግር ላይ እንደሚወድቁ የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

አርሶ አደሩ ለአባይ ግድብ ማሰሪያ፣ ለመለስ ፋውንዴሽን ማሰሪያ፣ ለብአዴን ጽ/ቤት ማሰሪያ፣ ለማዳበሪያና ምርጥ ዘር እየተባለ በሚጠየቀው ገንዘብ እየተማረረ ይገኛል።

መጪውን ምርጫ ተከትሎ ኢህአዴግ ለአርሶ አደሩ የማዳበሪያ እዳ ክፍያ ማራዘሚያ እንደሚያደርግ በምርጫ ማሸነፊያ ስትራቴጂው ላይ አስፍሯል።