ሱዳን በመቶዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ከአገሯ አስወጣች

ግንቦት ፳፩(ሃያ አንድ)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በካርቱም ሁዳ እየተባለ በሚጠራው እስር ቤት ከ800 በላይ የሚሆኑ ኢትዮጵያውያን የሚገኙ ሲሆን፣ ከእነዚህ መካከል 40 እስረኞች ሰሞኑን ከእስር ቤት ወጥተው ወዳልታወቀ ስፍራ መወሰዳቸውን ሱዳን የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ገልጸዋል።

ካርቱም አካባቢ የተሰበሰቡ  ከ600 በላይ ኢትዮጵያውያን ተጠርዘው ወደ አገራቸው መወሰዳቸውን እስካሁን ደረስ ኢትዮጵያ ይድረሱ አይደረሱ አልታወቀም።

የሱዳን ፖሊስ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እንደ አዲስ በጀመረውን ኢትዮጵያውያንን ወደ አገራቸው የመመለስ ዘመቻ፣ ቁጥራቸው በውል የማይታወቅ ሰዎች መሞታቸውንና ለአካል ጉዳት መዳረጋቸውን ኢትዮጵያውያን ገልጸዋል።

አንዳንድ ኢትዮጵያውያን ከ15 አመት ላላነሰ ጊዜ በሱዳን እስር ቤቶች እንደሚገኙ እነዚሁ ኢትዮጵያውያን ገልጸዋል።

የኢህአዴግ  መንግስት ተቃዋሚዎችን ይቀላቀላሉ ብሎ በመስጋቱ የሱዳን መንግስት በአገሪቱ ውስጥ የሚገኙና የገዢው ፓርቲ አባል ያልሆኑትን ዜጎች እንዲያስወጣለት መጠየቁ ይታወሳል። ሁለቱ አገሮች በቅርቡ በተፈራረሙት የጸጥታ ስምምነት የኢትዮጵያ ጦር እስከ ተወሰኑ ኪሎሜትሮች ወደ ሱዳን ድንበር ዘልቆ በመግባት ለጸጥታ ስጋት ይሆናሉ ብሎ የሚያስባቸውን ኢትዮጵያውያንን አፍኖ የመውሰድ ወይም ጥቃት የመሰንዘር ፈቃድ አግኝቷል።

በአገሪቱ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ኮሚሽነር አቤት ቢሉም አጥጋቢ መልስ ለማግኘት አልቻሉም።

በጉዳዩ ዙሪያ ሱዳን የሚገኘውን የኢትዮጵያን ኢምባሲ ወኪሎች ለማናገር ያደረግነው ጥረት አልተሳካም።