ከአዲስ አበባ ካርታ ጋር በተያያዘ የሚደረገው ተቃውሞ እንደቀጠለ ነው

ሚያዚያ ፳፫ (ሃያ ሦስት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የመስተዳድሩ  ባለስልጣናት ያወጡትን የከተማዋን አዲስ ማስተር ፕላን ተከትሎ በተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች የሚገኙ የኦሮሞ ተወላጆች የጀመሩት ተቃውሞ ወደ ተለያዩ ዩኒቨርስቲዎችና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች በመዛመት ላይ ነው። በአምቦ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ተማሪዎች በፌደራል ፖሊሶች ሲገደሉ በድሬዳዋ ደግሞ በመቶዎች የሚቆጠሩ ተማሪዎች ታስረዋል። በአዳማ የተጀመረው ተቃውሞ የረገበ ቢመስልም ውጥረቱ ግን አሁንም እንዳለ ነው።

ዛሬ ደግሞ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የ6 ኪሎ ተማሪዎች ተቃውሞ ለማድረግ እንቅስቃሴ በጀመሩበት ወቅት የዩኒቨርስቲው ሃላፊዎች ተማሪዎችን አነጋገርው ተቃውሞውን ጋብ እንዲል አድርገውታል። የክልሉ ባለስልጣናት በነገው እለት ተማሪዎችን ያነጋግራሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ለማወቅ ተችሎአል። በግንደ በረት የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ባስነሱት ተቃውሞም እንዲሁ በርካታ ተማሪዎች ተጎድተዋል።

ተማሪዎች አርሶደሮችን ከመሬታቸው በህገወጥ መንገድ ማፈናቀሉ እንዲቆም እየጠየቁ ሲሆን፣ የመንግስት ባለስልጣናት በበኩላቸው እቅዱ በአዲስ አበባ ዙሪያ ያሉ አርሶ አደሮች ከልማቱ ተጠቃሚ ይሆናል በማለት ህዝቡን ለማሳመን እየጣሩ ነው።

ይህ በእንዲህ እንዳለ የአሜሪካየውጪጉዳይሚኒስትርሚስተርጆንኬሪ  አዲስአበባበገቡበትዕለትበኢትዮጽያ የአሜሪካኤምባሲከአዲስአበባ እናኦሮሚያየጋራየማስተርፕላንጋርተያይዞበዩኒቨርሲቲተማሪዎች የተቀጣጠለውንተቃውሞመነሻበማድረግአሜሪካዊያንበተለይወደ አምቦአካባቢእንዳይጓዙመግለጫ አውጥቷል።

ኢምባሲው በአምቦ የተነሳውን ከፍተኛ ተቃውሞ ተከትሎ ወደ አካባቢው የሚሄዱ አሜሪካውያን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ አሳስቧል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ግንቦት7 የፍትህ ፣ የነጻነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ  የመንግስት የጸጥታ ሃይሎች በኦሮሞ ሕዝብና ወጣቶች ላይ እያካሄደው ያለውን አረመኔያዊ ጭፍጨፋ፣ እስርና አፈናን በጥብቅ አውግዟል። ህወሓት፣ ኦህዴድ እና በዚህ ጭፍጨፋ እጃቸው ያለበት ሁሉ ከተጠያቂነት የማያመልጡ መሆኑንም ገልጿል።

“የኦሮሚያ ወጣቶች በአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ስም የድሀ ገበሬዎች መፈናቀልን መቃወማቸው ፍትሀዊ ነው” ያለው ግንቦት7፣  የወያኔ “ማስተር ፕላኖች” የወያኔ የዘረፋ እቅዶች መሆናቸው በተደጋጋሚ የታየ ጉዳይ ነው ሲል አክሏል።

ወያኔ ኦሮሚያን ብቻ ሳይሆን መላዋን ኢትዮጵያ በምስለኔዎቹ አማካይነት እየገዛ የኢትዮጵያን ውድ ልጆች በራሳቸው ጉዳይ ባይተዋር አድርጓቸዋልሲል የሚኮንነው ግንቦት7፣  ወጣቶች በአካባቢያቸው ጉዳይ ብቻ ሳይሆን በመላው ኢትዮጵያ ጉዳይ እንደሚያገባቸው፣ ድምፃቸው ሊሰማ እንደሚገባ ገልጿል።

“የሌላው አካባቢም ወጣት የኦሮሚያ ገበሬ መፈናቀል እንደሚያገባው፣ ኢትዮጵያዊያን በኢትዮጵያ ውስጥ በሚደረግ ጉዳይ ሁሉ እንደሚያገባውና፣ በየትኛውም የኢትዮጵያ ክልል ውስጥ ወያኔ የራሱን እቅድ እንዲጭንብን አንፈልግም። ” ሲል አቋሙን አንጸባርቋል።

ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ፣ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ የኦሮሞ ወጣቶች ጥያቄ የመላው ኢትዮጵያ ሕዝብ ጥያቄ አድርጎ እንዲወስድም ጥሪ  አድርጓል።  ”

በጉራፈርዳና በቤንሻንጉል የተጀመረው መፈናቀል ዛሬ አዲስ አበባ አጎራባች ከተሞች ደርሷል። በአምቦ ይህንን የተቃወሙ ወጣቶች በግፍ ተጨፍጭፈዋል፤ በሌሎች ቦታዎችም ላይ ግድያውና እስሩ በርትቷል። ወጣቱ  የጥይት እራት ሆኖ እስኪያልቅ መጠበቅ አንችልም፤ ሁሉም ትግሉን ይቀላቀል።” ብሎአል።

በአንድ ወይም በሌላ መንገድ የወያኔን አምባገንነት የተቃወሙ በሙሉ የጥቃቱ ሰላባዎች ሆነዋል የሚለው ግንቦት7፣ ለሰልፍ ቅስቀሳ አደረጋችሁ በሚል የታሰሩ የሰማያዊ ፓርቲ ወጣቶች ሰልፉ ተደርጎ  ካለቀ በኋላም አለመፈታታቸውን ፣ ሀሳባቸውን በቲዩተር እና ፌስ ቡክ ማኅበራዊ ሚዲያዎች ሲገልጹ የነበሩ የዞን ዘጠኝ አባላት በአሸባሪ ድራማ በታጀበ ትዕይንት ወደ ማሰቃያ ሥፍራ ከተወሰዱ ቀናት መቆጠራቸውን” በመግለጽ ይህ ሰቆቃ ፣ ጭፍጨፋና አፈና ይቁም” ብሎአል።

አንድነት ፓርቲ ለኢሳት በላከው መግለጫም እንዲሁ በሰፊው የኦሮሞ ህዝብ እና ልጆች ላይ እየተፈፀመ ያለውን ግፍ በአጽንኦት እናወግዛለን ብሎአል።

“ምንም አይነት ህዝባዊ ውይይት ሳይደረግበት ከሰማይ ዱብ ያለው የአዲስ አበባ እና ኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ የልማት መሪ ፕላን ያስቆጣቸው የኦሮሞ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ሰልፍ በማድረጋቸው የደረሰባቸውን ህገ ወጥ ድብደባና እስራት” አንድነት በእጅጉ እንደሚቃወመው ገልጿል።

ተማሪዎቹ ለተቃውሞ አደባባይ ቢወጡ ተፈጥሯዊ እና ህገ መንግስታዊ መብታቸው ሊከበር በተገባ ነበር ያለው ፓርቲው፣ ነገር ግን ሁሉን ነገር ካልጋትኳችሁ የሚለውና ለዴሞክራሲያዊ ሽንፈት የማይገዛው ኢህአዴግ በተማሪዎቹ ላይ ያደረሰውን ጥቃት እንቃወማለን ብሎአል።

የታሰሩ ተማሪዎችም በአስቸኳይ እንዲፈቱ፣  የኦሮሞ ተማሪዎችን በገፍ ከዩኒቨርሲቲ የትምህር ገበታቸው በማባረር የሚታወቀው የኢህአዴግ መንግስት ከዚህ ተደጋጋሚ ተግባሩ ታቅቦ ልጆቹን በአስቸኳይ ወደ ትምህርት ገበታቸው እንዲመልስም ጠይቋል።በአጠቃላይ መሬት የዜጎች መያዣ መሆኑ እንዲቀር እንታገላለን ያለው አንድነት፣  ዜጎች በመሬታቸው የመደራደር እውነተኛ መብት ሊኖራቸው እንደሚገባ ተቃውሞ የሚያነሱ ዜጎችም ድምፅ እንዲሰማም አሳስቧል።