ኢትዮ ቴልኮም ግንቦት7 ን መሰለሉ ተጋለጠ

መጋቢት ፫ (ሶስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም 

ኢሳት ዜና:-በህወሐት ጄኔራሎች አመራር ስር የወደቀው ኢትዮ ቴልኮም ፊን ሰፓይ በተባለ ሶፍትዌር የግንቦት 7 ለፍትህ፣ ለነጻነትና ለዲሞክራሲ መረጃዎችን ሲሰልል መገኘቱን ተቀማጭነቱ አውሮፓ የሆነ አንድ አለማቀፍ የሶፍት ዌር ኩባንያ አጋልጧል።

ሞርጋን ማርኩዊስ ቦሪ፣ ቢል ማርዛክ ፣ ክላውዲዮ ጋርኔሪ እና ጆን ስኮት ሬይላተን ሲትዝን ላብ በተባለ ዌብሳይት ላይ ባወጡት ጽሑፍ ፣ ፊን ስፓይ የግንቦት 7ትን መሪዎች ፎቶግራፍ ወደ ኮምፒዩተር ተጠቃሚዎች በመላክ መረጃዎችን ለኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት ለማቀበል መሞከሩን ገልጸዋል።

ጉዳዩን በማስመልከት ቃለመጠይቅ ያደረግንላቸው የግንቦት7 ምክር ቤት ጸሀፊ አቶ አምሳሉ ጸጋየ ፣ የኢትዮጵያ መንግስት ከድርጅቱ መረጃዎችን ለመውሰድ ተደጋጋሚ ሙከራ ሲያደርግ እንደነበር መረጃዎች እንዳሉዋቸው ገልጸዋል

የግንቦት7  መረጃዎች ወደ መንግስት እጅ አለመግባታቸውን ያረጋገጡት አቶ አምሳሉ፣ ድርጅቱ በስልጣን ላይ ካለው መንግስታ ጋር ከፍተኛ የሳይበር ጦርነት ሲያድረግ እንደነበር ገልጸዋል

ጉዳዩን በማስመልከት ቃለ ምልልስ ያደረግንላቸው ኢንጂነር ጥላሁን ዝምታ ፣ ፊን ስፓይ  ወንጀለኞችን ለመያዝ ተብሎ የፍትህና የደህንነት ሰራተኞች እንዲጠቀሙበት በሚል መነሻ የተመረተ መሆኑን ገልጸው፣ አፋኝ መንግስታት ግን ሶፍትዌሩን ተቃዋሚዎችን ለመሰለል እንደሚጠቀሙበት ተናግረዋል

አብዛኞቹ የስለላ ሶፍትዌሮች የሚላኩት ፣ የሰዎችን ስሜት በሚይዙ ነገሮች መሆኑን የገለጹት ኢንጂነር ጥላሁን ፣ ህዝቡ በተለያዩ መንገዶች ከሚላኩ መልእክቶች እንዲጠነቀቅም መክረዋል።