አንድነት ፓርቲ በአራት ወራት ውስጥ 1 ሚሊዮን ብር ለመሰብሰብ አቅዷል

የካቲት ፮ (ስድስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ፓርቲው ለመገናኛ ብዙሀን ባሰራጨው መረጃ፣ ገንዘቡን የሚያሰባስበው፣ በመንግስት ቁጥጥር ስር ያለው ብርሀንና ሰላም ማተሚያ ቤት በህዝብ ዘንድ ተቀባይነት እያገኘ የመጣውን ፍኖተ-ነጻነት ጋዜጣን ለማተም ፈቃደኛ ባለመሆኑ የራሱን ማተሚያ ቤት ለማቋቋም ነው።

ፓርቲው ብቸኛ ልሳኑ የሆነውን ፍኖተ-ነጻነትን በመንግስት የአፈና ፖሊሲ የተነሳ ለማሳተም እንዳልቻለ ገልጿል። ይህንን ችግርም ለመቅረፍ ድርጅቱ በሚቀጥሉት አራት ወራት 1 ሚሊዮን የኢትዮጵያ ብር ለመሰብሰብ ማቀዱን አስታውቋል።

ፓርቲው ለነጻ ፕሬስና ለሚዲያ ነጻነት መምጣት የሚታገሉ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚገኙ  ኢትዮጵያውያን ድጋፍ እንዲያደርጉለት ጠይቋል። አንዳንድ መረጃዎች እንደሚያሳዩት በውጭ አገር ከ1 ሚሊዮን ያላነሱ ኢትዮጵያውያን ይኖራሉ።

አንድነት ፓርቲ ብቸኛ ልሳኑ በመንግስት ቢታፈንበትም መረጃዎችን በኢንተርኔት እያሰራጨ እንደሚገኝ ይታወቃል።