ሰማያዊ ፓርቲ የህግ የበላይነት ጭላንጭል እየተዳፈ ነው አለ

የካቲት ፮ (ስድስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ፓርቲው ባወጣው መግለጫ  መንግስት ከሙስሊም ጥያቄ አቅራቢዎች ተወካዮች ጋር ሲወያይ ከቆየ በሁዋላ አብዛኞቹን በሽብረተኝነት ከሶ ወደ እስር ቤት እንዲወርዱ ማድረጉንና ክሳቸውም እየታየ ባለበት ወቅት በህገ መንግስቱ የተደነገገውን ማንም ሰው ወንጀለኛነቱ በፍርድ ቤት እስኪረጋገጥ ድረስ እንደንጹህ የመቆጠር መብትን በመታገስና ተከሳሾች ራሳቸው ጥፋተኞች መሆናቸውን እንዲያረጋግጡ በሚያስገድድ ሁኔታ የዞጎችን ስእብና የሚያራክስ ዘጋቢ ማሳየቱን ገልጿል።

ፓርቲው ፣ መንግስት በህግ ስር በሚገኙ ዜጎች ላይ በተደጋጋሚ የፈጸማቸውን አሳፋሪ ድርጊቶች በማየት፣ በስራ አስፈጻሚው አካል ለህግ አልገዛም ባይነት ሲሰፍን ዜጎች በህግ ላይ ያላቸው እምነት እንዲሸረሸር እያደረገው መሆኑን በመገንዘብ እንዲሁም በሀገራችን ለብዙ ዘመናት ተቻችለው የኖሩትን ዜጎች እርስ በርሳቸው እንዳይተማመኑ የሚያደርግ ስራ እየተሰራ በመሆኑ ድርጊቱን ኮንኗል።

በርካታ የፖለቲካ ድርጅቶች መንግስት በቅርቡ ያሰራጨውን ጀሀዳዊ ሀረካት ፊልም ማውገዛቸው ይታወቃል።