በገንዳሆ ከተማ በህዝቡና በፖሊስ መካከል በተፈጠረ ግጭት 4 ሰዎች ተገደሉ

ሚያዚያ ፳፩ (ሃያአንድ)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በሰሜን ጎንደር ዞን በመተማ ወረዳ በገንዳሆ ከተማ አንድ በጉምሩክ በኩል ውክልና ያለው የፌደራል ፖሊስ አንዱን የባጃጅ ሹፌር ” ኮንትሮባንድ ጨርቅ ጭነሃልና ጉቦ ሰጥተኸኝ እለፍ” በማለቱና ሾፌሩም “ለዚህ ለማይረባ ጨርቅ ጉቦ አልከፍልህም” የሚል መልስ በመስጠቱ ፖሊሱ ሾፌሩን ተኩሶ መግደሉን የአካባቢው ነዋሪዎች ለኢሳት ገልጸዋል።

በድርጊቱ የተበሳጨው የገንዳውሃ ህዝብ ወደ ወረዳው ፖሊስ ጣቢያ በመሄድ  ገዳዩ ለፍርድ እንዲቀርብ ጠይቋል።  የወረዳው ፖሊስ ጽ/ቤትም “ጉዳዩ እኛን አይመለከትም ወደ ፌደራል ፖሊስ ሄዳችሁ ጠይቁ” የሚል መልስ መስጠቱን ነዋሪዎች ተናግረዋል።

ህዝቡ ወደ ፌደራል ፖሊስ ጽ/ቤት በሚሄድበት ጊዜ ፣ ፖሊሶች በከፈቱት ተኩስ 3 ሰዎች ወዲያውኑ ሲገደሉ፣ 3 ሰዎች ደግሞ በጽኑ ቆስለው ወደ ጎንደር ሆስፒታል ተወስደዋል።

ውጥረቱ አሁንም እንዳለ ሲሆን፣ የአካባቢው  ህዝብ በነገው እለት ተቃውሞ ለማድረግ እየተዘጋጀ መሆኑን ነዋሪዎች ለኢሳት ገልጸዋል

በጉዳዩ ዙሪያ የወረዳውን ፖሊስ ለማነጋገር ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም።