የሰማያዊ ፓርቲ ወጣት አመራሮችና ደጋፊዎች በዋስ እንደማይፈቱ አስታወቁ

ሚያዚያ ፳፩ (ሃያአንድ)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የፓርቲውን ምክትል ሊ/መንበር አቶ ስለሺ ፈይሳንና የህዝብ ግንኑነት ሃላፊውን ብርሃኑ ተክለያሬድን ጨምሮ ከ20 በላይ አመራሮችና ደጋፊዎች ትናንት ፍርድ ቤት ቀርበው ፣ ፍርድ ቤቱ ፖሊስ ክስ እንዲመሰርት ወይም እስረኞቹ በዋስ እንዲለቀቁ ቢያዝዝም እስረኞቹ ሃሳቡን ሳይቀበሉት ቀርተዋል። እስረኞቹ “ሰልፉ ህጋዊ እውቅና አግኝቶ በመገናኛ ብዙሃንም የተዘገበ በመሆኑ ፖሊስ ህገወጥ ሰልፍ አድርገዋል በሚል ለፍርድ ቤቱ ያቀረበው ክስ ተቀባይነት የለውም ፣ በነጻም ልንፈታ ይገባል” በማለት መከራከሪያ በማቅረባቸው ምንም ውሳኔ ሳይሰጥበት  ወደ እስር ቤት እንዲመለሱ ተደርጓል።

የአመራሮችና ደጋፊዎች መታሰር በተቃውሞ ሰልፉ ላይ ተጽእኖ ነበረው ወይ ተብለው የተጠየቁት የፓርቲው ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል፣ የመንግስት አፈና ተጽእኖ እንደነበረው ገልጸው፣ ይሁን እንጅ መረጃ የደረሰው ህዝብ ሰልፉን መቀላቀሉንና ድምጹን ማሰማቱን ገልጸዋል።

“ፓርቲዎ የቀለም አብዮት ለማስነሳት እየሰራ ነው በሚል ከኢህአዴግ መንግስት ክስ ይቀርብበታል ፣ ምልሽዎ ምንድነው?” ተብለው የተጠየቁት ኢ/ር ይልቃል፣  ፓርቲያቸው ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር እንዲኖር እንደሚፈልግ እና የቀለም አብዮት የማስነሳት እቅድ እንደሌለው ገልጸው፣ “ኢህአዴግ አገሪቱን መምራት ባለመቻሉ ግራ ተጋብቶ፣ እሱም የማይወደውን እኛም የማንወደውን እንድናደርግ እየገፋፋን ነው” ብለዋል።

ከኢ/ር ይልቃል ጌትነት ጋር የተደረገው ቃለምልልስ ከመጨረሻው ዜና በሁዋላ እንደሚቀርብ ለመግለጽ እንወዳለን።