በድሬዳዋ፣ ሀርርና ጅጅጋ የተፈጠረው የኤሌክትሪክ መቋረጥ በምሰሶዎች ላይ በተፈጠረ ስርቆት ነው ተባለ

ጥቅምት ፮ (ስድስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-መንግስት እንዳስታወቀው ወለንጨቲ አካባቢ በኤሌትሪክ ምሶሶ ላይ በተፈጸመው ዝርፊያ  5 ምሶሶዎች ወድቀዋል። በዚህም የተነሳ ካለፈው ሳምንት ጀምሮ በ ድሬዳዋ፣ ሀረርና ጅጅጋና በሌሎችም ትልልቅ ከተሞችና የገጠር መንደሮች ኤሌትሪክ ተቋርጦባቸዋል።

በኤሌክትሪክ የሚሰሩ ስራዎች እንዲቋረጡም ከማስገደዱ በተጨማሪ በኤሌትሪክ የሚሰሩ የውሀ ፓንፖች ስራቸውን በማቋረጣቸው  የአካባቢው ነዋሪዎች መቸገራቸውን መንግስት አምኗል።

በወለንጨቲ የተፈፀመው የኤሌትሪክ ምሰሶ ስርቆት ከ35 ሚሊዮን ብር በላይ በንብረትና መልሶ ጥገና ላይ ወጪ እንደሚያስወጣ መንግስት አስታውቋል። መንግስት ችግሩን በሚቀጥሉት ሁለት ቀናት ውስጥ እንደሚፈታ አስታውቋል።

በኢትዮጵያ ውስጥ በኤሌክትሪክ ምሰሶዎች ላይ ተደጋጋሚ ስርቆት እንደሚፈጸም ይታወቃል። ምሁራን  ለስርቆት መባባስና ለወንጀል መበራከት ዋናው ምክንያት የኑሮ ውድነት ነው ይላሉ።