አቦይ ስብሀት የፊታችን ኦክቶበር 20 ጀርመን ይመጣሉ

ጥቅምት ፮ (ስድስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የህዝባዊ ወያነ ሀርነት ትግራይ (ህወሀት)መስራች አባል የሆኑትን በአቶ መለስ ጊዜ ከከፍተኛ የድርጅቱ ቦታዎች ተገፍተው የቆዩት አቶ ስብሀት ነጋ እንደ ፈረንጆቹ አቆጣጠር በመጪው መስከረም 20 በጀርመን-ቡንደስታግ ተገኝተው ንግግር እንደሚያደርጉ ተመለከተ።

በነባሮቹ የድርጅቱ አባላት ዘንድ <አቦይ>ተብለው የሚጠሩት አዛውንቱ አቶ ስብሀት ነጋ የአቶ መለስ ዜናዊን ሞት ተከትሎ  በድርጅቱ ውስጥ ወደ ቀድሞ ተሰሚነታቸውና አድራጊ ፈጣሪነታቸው እየተመለሱ እንደሆነ የኢህአዴግ ከፍተኛ ካድሬዎች ለኢሳት ገልጸዋል።

ከሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር እና ከባለቤታቸው ወይዘሮ አዜብ መስፍን ጋር ከፍተኛ ቅራኔ በመፍጠራቸው ከኢፈርት ዋና ሥራ አስኪያጅነታቸው ተወግደው  የኢትዮጵያ-የሰላምና የልማት ዓለማቀፍ ኢንስቲትዩት  ወደሚባል ተራ ቢሮ ተወርውረው አድፍጠው  የቆዩት አቶ ስብሀት፤ የአቶ መለስን ሞት ተከትሎ የተሰጣቸው ስልጣን ባይታወቅም  በአገሪቱ የወደፊት አቅጣጫ ዙሪያ ቀዳሚው ተናጋሪና ወሳኝ ሰው ሆነው ብቅ ብለዋል።

በመጪው ኦክቶበር 20 በጀርመን -ቡንደስታግ የሚመጡትም ሆነ የሚናገሩት በምን <ካፓሲቲ> እንደሆነ አልታወቀም።

አቶ ስብሀት ወደ ጀርመን ይመጣሉ መባልን የሰሙ አንዳንድ ኢትዮጵያውያን በየፌስቡክና በየ ትዊተር ገፆቻቸው፦ <ልንቃወማቸው ይገባል>የሚል አስተያዬት እየሰጡ ቢሆንም፤በተደራጀ መልክ የተቃውሞ ሰልፍ  ስለመኖሩ እስካሁን ማረጋገጥ አልተቻለም።