በየረር ባሬ ከተፈጠረው ግጭት ጋር በተያያዘ መምህራን ታሰሩ

ሚያዚያ ፩ (አንድ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በሶማሊ ክልል ነዋሪ የሆኑ የየረር ጎሳ አባላት ከአስተዳደር ጋር በተያያዘ ያነሱዋቸውን ጥያቄዎች ተከትሎ በተለያዩ ትምህርት ቤቶች የሚማሩ 16 የጎሳው አባላት መታሰራቸውን የአካባቢው ነዋሪዎች ለኢሳት ገልጸዋል።

ከወራት በፊት በክልሉ መስተዳድር ትእዛዝ ልዩ ሚሊሺያ እየተባለ የሚጠራው ሃይል በጎሳው አባላት ላይ በከፈቱት ጥቃት ከ50 ያላነሱ ሰዎች መገደላቸውን ቀደም ብሎ በኢሳት የተዘገበ ሲሆን፣ ድርጊቱ ተጣርቶ እርምጃ እንዲወሰድላቸው ለጠ/ሚ ሃይለማርያም ደሳለኝ ለማሳወቅ ወደ አዲስ አበባ የሄዱ 19 የአገር ሽማግሌዎች ካለፉት 2 ወራት ጀምሮ የታሰሩ ሲሆን እስካሁን አልተፈቱም።

ከ60 እስከ 85 እድሜ ያላቸው የአገር ሽማግሌዎች ህክምና ሳይቀር ተነፍገው ከእስር ቤት እስር ቤት እየተዘዋወሩ እንዲታሰሩ በመደረጉ ህዝብ ለመጠየቅ እንደተቸገረ ነዋሪዎች ይገልጻሉ።

አንዳንድ የጎሳው አባላት ወደ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤ እና በመንግስት በሚደገፈው የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን በመሄድ አቤት ያሉ ሲሆን፣ በመንግስት የሚደገፈው ኮሚሽን ከትናንት በስቲያ ወደ አካባቢው በመጓዝ ህብረተሰቡን አነጋግሯል። ኮሚሽኑ በልዩ ሚሊሺያው የተገደሉ ሰዎችን ቁጥር ለማወቅ ህዝቡን በጠየቀበት ወቅት፣ ህዝቡ በአንድ ድምጽ የአወንታ ቃሉን መስጠቱን፣ ኮሚሽኑም ሁኔታውን መረዳቱን ለህዝቡ በመግለጽ መመለሱን በስፍራው የነበሩ ሰዎች ለኢሳት ገልጸዋል።

የሰብአዊ መብቶች ጉባኤ በበኩሉ ግድያውን እንደሚያጣራና መግለጫ እንደሚያወጣ ለማወቅ ተችሎአል።

ሰሞኑን እየታደኑ የታሰሩትን መምህራን ጨምሮ 35 የጎሳው አባላት ታስረዋል።

በጉዳዩ ዙሪያ የሶማሊ ክልል ፖሊስ ኮሚሽነርን ለማነጋገር ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም።