በኣዲስ ኣበባ ከባለቤቶቹ ፈቃድ ውጪ የቅዱስ ቂርቆስ መካነ መቃበር እየታረሰ ነው

መጋቢት ፮ (ስድስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም 

ኢሳት ዜና:-ከፒያሳ  እስከ ጎፋ ካምፕ ድረስ ሊሠራ ከታሰበው የመንገድ ሥራ ፕሮጀክት ጋር በተያያዘ፥ የ ቅዱስ ቂርቆስ መካነ መቃብር ስፍራ ከሙታን ቤተሰብ አውቅና ውጭ  እየታረሰ እና የሙታን ኣጽምም  ከአፈር ጋር እየታፈሰ ወጣ ወዳለ ስፍራ እየተጣለ እንደሆነ ታውቋል።

ነዋሪዎቹ እንደተናገሩት በልማት ስም እየተካሄደ ያለውን ይህን ዘግናኝ ድርጊት እያስፈፀመ ያለው  የመንገድ ሥራውን በበላይነት እየሠራ ያለው  የመንገዶች ባለስልጣን ነው።

የዚህ ዓይነቱ ድርጊት ካለፉት አራት ቀናት ወዲህ በማናለብኝነት እየተፈፀመ እንደሚገኝ  የገለጹት ነዋሪዎቹ ፤ ወዳጅ ዘመዶቸቸውን በመካነ-መቃብሩ ቀብረው የነበሩ  የሙታን ቤተሰቦች እየተፈፀመ ያለውን ድርጊት  ከሰሙበት ሰዓት ጀምሮ ከተለያዩ መንደሮች አየተጠራሩ ፥የቻሉ መቃብሩን በማስነሳትና ቅሪተ አካሉን በማስወጣት  ወደ ደብረ ሊባኖስ…ለማስቀበር ሲያስወስዱ…ያልቻሉት ደግሞ  እዚያው  ቂርቆስ ቤተክርስቲያን ግቢ ውስጥ ባሰሩት ጊዜያዊ  የ ዐጽም ማከማቻ  ቆርቆሮ ውስጥ ለማከማቸት  መገደዳቸውን አመልክተዋል።

ከነዋሪው እውቅና ውጪ የመቃብር ቁፋሮው በሚካሄድበት ወቅት ረብሻ እንዳይነሳ በሚል ስጋት ፥ሲቪል የለበሱ ወታደሮች  በስፍራው መገኘታቸውን የገለፁት ነዋሪዎቹ፤፥የቁፋሮውን ማሽን የሚያንቀሳቅሰው ግለሰብም  ፊቱ እንዳይታይ ሙሉ በሙሉ ተሸፋፍኖ እንደነበርም  ተናግረዋል።

የዓይን እምኞች እንደሚሉት፡ ከሁሉ የሚያሳዝነው ፥ከአፈር ጋር ኣብሮ ሲቆፈር እና በገልባጭ መኪኖች ላይ ሲጫን የነበረውን የሰዉ ልጅ ቅሪት የተቀላቀለበትን አፈር ፥ኣንዳንድ የኣካባቢው ነዋሪዎች ፈጽሞ ባለማወቅ ለጭቃ ቤታቸው ማሳደሻ እና ማሰሪያ በሚል በየቤታቸው በራፍ የማስደፋታቸው ጉዳይ ነበር ።በተለይም ግሎባል ሆቴል ፊት ለፊት ፥በተለምዶ ኣርባ ቀበሌ  ተብሎ የሚጠራው ሰፈር መንደርተኞች ያለማወቅ  ይህን ነገር ሲያደርጉ ነበር ።

ይሁንና ፤እማኞቹ እንደሚሉት  ነዋሪዎቹ  ወደ ሁዋላ ላይ ከመጣላቸው ኣፈር ጋር የሰው ልጅ ራስ ቅልን ጨምሮ ረጃጅም ኣጥንቶችን ከኣፈሩ ጋር ተደባልቆ በማየታቸው እጅግ ተደናግጠው ኣፈሩን መልሶ ለማስወሰድ ለማን ኣቤት እንደሚሉ ግራ ተጋብተውም ሲጯጯሁ ተስተውለዋል።

በተመሣሳይ ከቀናት በፊት                                            በቦሌ ክፍለ ከተማ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ 200 አባወራዎች ለዘመናት ከኖሩበት ህጋዊ ይዞታቸው በግዳጅ መፈናቀላቸው ይታወሳል።

እጅግ አሳዛኙና  አስገራሚው ነገር ነዋሪዎቹ በቦሌ ውስጥ ያለውን ይዞታቸውን እንዲለቁ የተደረገው በካሬ ሜትር የ 18 ብር ካሳ ታስቦላቸው መሆኑ ነው።

ተፈናቃዮቹ ብቻ ሳይሆን ጉዳዩን በቅርበት የተከታተሉ ወገኖች ጭምር በካሬ ሜትር በመቶ ሺዎች ብር በሚጠየቅበት በቦሌ ክፍለ ከተማ የሚገኝን ይዞታ በካሬ ሜትር 18 ብር እያሰቡ ልቀቁ ማለት ምን ዓይነት ዘግናኝ ግፍ ነው? በማለት ሀዘናቸውን ለኢሳት  ገልጸዋል።

በወቅቱ የምንዛሬ ተመን መሰረት 18 ብር ማለት   0. 75 ዩሮ ሳንቲም መሆኑን፤ ዓለማቀፍ  የምንዛሬ መለወጫዎች ያመለክታሉ።