በኢትዮጵያ 8 በመቶ የሚሆኑ ህጻናት ብቻ ንጽህናቸው እንደሚጠበቅላቸው ዩኒሴፍ አስታወቀ

መጋቢት ፲፫ (አስራ ሦስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም 

ኢሳት ዜና:-ድርጅቱ የአለም የውሀ ቀንን ምክንያት በማድረግ ባወጣው መግለጫ በኢትዮጵያ ከአምስት አመት በታች ያሉ ህጸናት በአብዛኛው ከውሀ ንጽህና ጋር በተያያዘ እንደሚሞቱ ገልጿል። በኢትዮጵያ የዩኔሴፍ የአስቸኳይና የመስክ ጥናት ቡድን ሀላፊ የሆኑት ሳንጃይ ዊስኬራ ሲናገሩ ” ቁጥሮችን ስንጠቅስ ትክክለኛውን የህጻናትን ፊት ማየት አለብን፣ አንዳንድ ጊዜ በትልልቅ ቁጥሮች ላይ እናተኩራለን፣ ከእነዚህ ትልልቅ ቁጥሮች ጀርባ ስለሚያልቁት ሰዎች ግን አንናገርም። በየቀኑ 90 ህጻናትን የጫኑ አውቶቡሶች ቢጋጩና ህጻናቱን ቢገድሉ ትልቅ ዜና ይሆናል፣ አሁን በአለም ላይ ከውሀ ንጽህና ጋር በተያያዘ እየሆነ ያለው ግን ይህ ነው” ብለዋል።
በኢትዮጵያ ከአምስት አመት በታች ከሚሞቱ ህጻናት 22 በመቶው የሚሞቱት ከውሀ ንጽህና ጋር በተያያዘ በሚፈጠር ተቅማጥ ነው። በቤንሻንጉል ጉሙዝና በጋምቤላ ችግሩ አስከፊ መሆኑንም ሪፖርቱ አመልክቷል። ኢትዮጵያ 62 በመቶ የሚሆነው ህዝብ በፈረንጆች አቆጣጠር በ2015 ንጹህ ውሀ እንዲያገኝ ለማድረግ እየጣረች መሆኑን የገለጸው ዩኒሴፍ፣ በ2011 በተደረገው ጥናት 54 በመቶው ህዝብ የንጹህ ውሀ ተጠቃሚ መሆኑን ገልጿል።

ይሁን እንጅ ይላል ዩኒሴፍ 8 በመቶ የሚሆነው ኢትዮጵያ ብቻ ነው ንጽህናው በተጠበቀ ሽንት ቤት መጠቀም የሚችለው። የንጹህ ሽንት ቤት እጥረት በመላው አገሪቱ የሚታይ መሆኑን የገለጸው ዩኔሴፍ፣ በተለይ ሴት ተማሪዎች በከፍተኛ ሁኔታ መቸገራቸውን ገልጿል።