ከአምስት ዓመት በፊት በሕግ የፈረሰውን የኢትዮጽያ ዜና አገልግሎት ድርጅት እንደገና ወደነበረበት ለመመለስ ዕቅድ መኖሩን ምንጮች ጠቆሙ

መጋቢት ፲፫ (አስራ ሦስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም 

ኢሳት ዜና:-የቀድሞ ማስታወቂያ ሚኒስቴርን መፍረስ ተከትሎ ግልጽ ባልሆነ ምክንያት እንዲፈርስ የተደረገው የቀድሞ መንግስታዊ
ዜና አገልግሎት በአሁኑ ወቅት በአቶ በረከት ስምኦን በሚመራው የመንግስት ኮምኒኬሽን ጽ/ቤት በአንድ መምሪያ ስር
በሕግ ባልተሰጠው ስም “የኢትዮጽያ ዜና አገልግሎት-ኢዜአ” በሚል ዜናዎችን በመስራት ለመንግስት መገናኛ ብዙሃን
በመሸጥ ላይ መገኘቱ ብዙዎችን ግራ የሚያጋባ ሆኗል፡፡

የመንግስት ኮምኒኬሽን ጽ/ቤት እያካሄደ ባለው የሪፎርም ስራ ውስጥ መ/ቤቱ ወደቀድሞ አደረጃጀቱ እንዲመለሰ
ታሶቦ እየተሰራ መሆኑ ታውቋል፡፡

ዜና አገልግሎት ያለአንዳች ምክንያት እንዲፈርስ የተደረገው የኢህአዴግ ኢንዶውመንት የሆነውንና በተመሳሳይ ሥራ
ላይ የተሰማራውን የዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከልን ለማጠናከር ታስቦ እንደነበር ጉዳዩን የሚያዉቁ ይናገራሉ።

በአሁኑ ወቅት  የቀድሞ ዜና አገልግሎት ድርጅት እጅግ በተዳከመ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኝም ይታወቃል፡፡

የዜና አገልግሎት እንደገና መቋቋም ብቻውን ለድርጅቱ ትንሳዔን እንደማያመጣ አንድ የድርጅቱ ባልደረባ ጠቅሰው
ድርጅቱ ውጤታማ እንዲሆን መንግስት እጁን በማንሳት የኤዲቶሪያል ነጻነቱ ተጠብቆ ሊሰራ ይገባል ብለዋል፡፡ከዚህ ውጪ ራሱን
የቻለ ተቋም መሆኑ ብቻ የሚያስገኝለት ፋይዳ የለም ሲል አክሏል።

ኢዜአ በህግ እንዲፈርስ ቢደረግም፣ ያለህጋዊ ፈቃድ ስራውን እስካሁን ድረስ ሲያከናውን ቆይቷል።