በአንዋር መስኪድ ከፍተኛ የጸጥታ ጥበቃ መካሄዱ ታወቀ

መጋቢት ፲፫ (አስራ ሦስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም 

ኢሳት ዜና:-በዛሬው እለት በአንዋር መስጊድ ከስግደት በሁዋላ የተለመደው መንግስትን የመቃወም ትይንት ይካሄዳል ብሎ የሰጋው ኢህአዴግ  በርካታ የአዲስ አበባ፣ የፌደራል ፖሊሶችን እና የደህንነት ሀይሎችን ቢያሰማራም ህዝቡ ስግደቱን አካሂዶ በሰላም ተበትኖአል።

ፖሊሶች ተቃውሞ ይደረጋል የሚል መረጃ በማግኘታቸው በርካቶች የአድማ በታኝ ልብሶችን ለብሰው በትልልቅ መኪኖች ውስጥ ሆነው ትእዛዝ ይጠብቁ እንደነበር የአዲስ አበባው ዘጋቢያችን ገልጿል።

ከትናትን ማታ ጀምሮ የደህንነት ሀይሎች ከኢህአዴግ ካድሬዎች ጋር በመሆን አንዳንድ የሙስሊም ወጣቶችን የተቃውሞ ድርጅቱን የሚያስተባብሩትን እና በህቡእ ተቃውሞ እንዲካሄድ  ትእዛዝ የሚያስተላልፉትን የታሳሪ ሙስሊም ኮሚቴዎች ተወካዮችን እንዲያሳውቁ በጥቅማጥቅሞች ለመደለል፣  ለማስፈራራት እና ለመሸንገል መሞከራቸውን ለማወቅ ተችሎአል።

በአብዛኛው የተጠየቁት ሙስሊም ወጣቶች የንግድ ድርጅቶች ያሉዋቸው ሲሆኑ ፣  አላማውም  የተቃውሞ ትእዛዝ አስተላላፊዎችን በመያዝ ትግሉን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማቆም መሆኑን የአዲስ አበባ የኢህአዴግ ጽህፈት ቤት ምንጮችን በመጥቀስ ዘጋቢያችን ሪፖርቱን አጠናቅሯል።

” ትናትን ማታ አንድ ካድሬ አንድ ከማላውቀው ሰው ጋር መጥቶ ማነው ትእዛዝ የሚያስተላልፍላችሁ በማለት አፋጠጠኝ” ያለ አንድ  የመርካቶ አካባቢ ሙስሊም ወጣት፣ “ለእኔ ማንም ትእዛዝ በስልክም ሆነ በኢሜል የሚያስተላልፍልኝ የለም” በማለት መመለሱን ፣ አብሮ የነበረው የደህንነት ሰው ግን ” በስልክ መልእክት እንደሚላክልህ ደርሰንበታል ሰዎችን ብትነግረን በስራህም በንግድህም እንጠቅምሀለን” በማለት እንደመከረው ለዘጋቢያችን ገልጿል።

በኢህአዴግ መንግስትና በሙስሊሞች መካከል የአይጥና ድመት ጨዋታ የተጀመረ ይመስላል በማለት አንድ ሙስሊም ወጣት አስተያየቱን ሰጥቷል።

ኢህአዴግ ከአንድ አመት በላይ የቆየውን የሙስሊሞች ጥያቄ ለምፍታት ባለመቻሉ ወደ ሀይል እርምጃ ሊገባ እንደሚችል ብዙዎች ቢገምቱም እስካሁን ድረስ በድፍረት እርምጃውን ሲወስድ አልታየም። ኢህአዴግ በአንዳንድ አካባቢዎች የሀይል እርምጃ ቢወስድም በተለይ የተቃውሞው ማእከል በሆነው አዲስ አበባ የሀይል እርምጃ ቢወስድ በራሱ ላይ ቤንዚን እንደማርከፍከፍ እንደሚቆጠርበት አስተያየት የሚሰጡ ወገኖች በርካታ ናቸው።

ሙስሊም የኢህአዴግ አባላት ድርጅታቸው በሚከተለው አቋም ሙሉ በሙሉ ደስተኛ አለመሆናቸውን መዘገባችን ይታወሳል።