በደቡብ ክልል ለአቤቱታ የመጡ ዜጎች ታገቱ

መጋቢት ፲፫ (አስራ ሦስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም 

ኢሳት ዜና:-የተለያዩ የመብት ጥያቄዎችን ለመጠየቅ በደቡብ ክልል በቁጫ ወረዳ ለአቤቱታ የወጡ ከ1000 ያላሱ ሰዎች በፖሊስ ታግተው መዋላቸውን የአካባቢው ሰዎች ለኢሳት ተናግረዋል።

ከፍትህ ፣ ከመልካም አስተዳዳር እና ከመብት ጋር በተያያዘ በርካታ ጥያቄዎችን ላለፉት 8 አመታት ሲያቀርቡ የቆዩት የቁጫ ወረዳ ነዋሪዎች ፣ 7 ወኪሎቻቸው መታሰራቸውን በመቃወም ትናንት አቤቱታ ለማቅረብ ሲሰባሰቡ በፌደራል ፖሊሶች ታግተዋል። የታሰሩና ድበደባ የደረሰባቸው ሰዎች መኖራቸውም ታውቋል።

ጉዳዩን በማስመልከት ጥያቄ የቀረብንላቸው የአንድነት ፓርቲ የደቡብ ክልል ተወካይና የምክር ቤት የሆኑት አቶ ዳንኤል ሽበሺ በክልሉ በተለያዩ ወረዳዎች የሚታየው ችግር የቆየ መሆኑን ገልጸው፣ የትናንትናው ተቃውሞ የሽማግሌዎች መታሰር መሆኑን ገልጸዋል

አቶ ዳንኤል በሰላም በር የታሰሩት ሰዎች ህዝብን ታነሳሳለችሁ ተብለው መታሰራቸውን ገልጸው በአጠቃላይ በክልሉ ያለው የመልካም አስተዳደርና ፍትህ እጦት መባባሱን አክለዋል።

የአገር ሽማግሌዎች ለምን ታሰሩ? ለአቤቱታ የመጡ ሰዎችስ ለምን ታገቱ በማለት ጥያቄ ያቀረብንላቸው ወረዳው ፖሊስ አዛዥ ሻለቃ አኒሳ ፣ ሰዎቹ ጥያቄ ያቀረቡበት መንገድ አግባብ አይደለም በሚል መታሰራቸውን አምነው፣ ሰልፈኞቹ የመጡበት መንገድ ተገቢ ባለመሆኑ እንደመለሱዋቸውም ተናግረዋል