በተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች የተካሄዱት የፖለቲካ ስልጠናዎች ውጤት አለማምጣታቸውን ተማሪዎች ገለጹ

ነሃሴ ፳፮(ሃያስድስት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ኢህአዴግ ከተለያዩ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ጋር ያደረገው የመጀመሪያ ዙር ውይይት የተፈለገውን ውጤት

አስገኝቶለታል ብለው እንደማያስቡ ኢሳት ያነጋገራቸው ተማሪዎች ገልጸዋል።

መጪውም ምርጫ አስታኮ የተሰጠው የፖለቲካ ስልጠና በተማሪዎች እና በኢህአዴግ ባለስልጣናት መካከል ያለውን አለመግባባት ያሳየና ተማሪዎች በስርአቱ

ላይ አመኔታ እንደሌላቸው የሚያመለክት መሆኑነ ተማሪዎች ግልጸዋል።

በደብረማርቆስ ዩኒቨርስቲ የመጀመሪያው ዙር ስልጠና መጠናቀቁን በማስመልከት ጥያቄ ያቀርበንለት ተማሪ ለኢሳት እንደገለጸው በሁለት ሳምንት ስልጠና አራት

ጉዳዮች ተነስተው ሰፊ ክርክር ተደርጎባቸዋል። ከታሪክ ጋር በተያያዘ መንግስት የሚያነሳው ጉዳይ፣ አማራውንና ኦሮሞውን ለማጋጨት ከመሞከር በተጨማሪ

ማራው በራሱ ታሪክ አፍሮ እንዲቀመጥ ለማድረግ የታቀደ ነው በሚል ተማሪዎች አጥብቀው ኮንነውታል። በኢህአዴግ በኩል ታሪካችን ነው ተቀበሉት በሚል

ለማግባባት ቢሞከርም አብዛኛው ተማሪ ሳይቀበለው ቀርቷል።

የሰብአዊ መብቶች ጥሰት፣ የፍትህ እጦት፣ የፕሬስ ነጻነት እንዲሁም የኢኮኖሚው ችግር ሰፊ ክርክር ያስነሳ እንደነበር ተማሪው አክሎ ገልጿል። ተማሪው እንደሚለው

90 በመቶ የሚሆነው ሰልጣኝ በኢህአዴግ ላይ ተቃውሞውን የገለጸ በመሆኑ፣ ኢህአዴግ በዚህ ዝግጅት ተጎጂ እንጅ ተጠቃሚ ነው ብሎ እንደማያስብ ተናግሯል

በአርባ ምንጭ ዩኒቨርስቲ ስልጠናውን ያከናወነው ሌላው ተማሪም ተመሳሳይ ሃሳብ አለው። የተዘጋጁት መድረኮች በሙሉ የተቃውሞ ማስተናገጃ ከመሆናቸው በተጨማሪ

ተማሪው ሲያነሳቸው የነበሩት ቅራኔዎች በበቂ ሁኔታ አለመመለሳቸው ተማሪውን ለበለጠ ብስጭት መዳረጉን ገልጿል።

በአርባምንጭ ውይይት ከታሪክ ጋር በተያያዘ ከተፈጠረው ውዝግብ በተጨማሪ ኢህአዴግ በተቃዋሚዎች ላይ ሰነዘረው አስተያየት ሌላ የውዝግብ መንስኤ ሆኖ ነበር።

የኢህአዴግ አወያዮች በኢትዮጵያ ስልጣን ሊረከብ የሚችል ተቃዋሚ ባልተዘጋጀበት ሁኔታ ፣ ኢህአዴግ የሚቀጥሉትን 50 አመታት በስልጣን ላይ ለመቆየት

እንደሚገደድ ገልጸዋል።

ተማሪው እንደሚለው ወደ ጠረፍ አካባቢ የሚኖሩ ተማሪዎች በውይይቱ ላይ መሳተፋቸው ስለአገራቸው እንዲውቁ ቢያደርጋቸውም፣ አብዛኞቹ በመረጃ እጥረት ያላወቁትን፣

ተማሪዎች ከሚያነሱዋቸው ጥያቄዎች እየሰሙ ብዙ ነገሮችን እንዲያዉቁ አድርጋቸዋል ብለዋል።

በድሬዳዋ ዩኒቨርስቲ በነበረው ስልጠናም እንዲሁ ከፍተኛ ውዝግብ የነበረበትና ከመነሻው እስከ መጨረሻው በአለመግባባት የተጠናቀቀ መሆኑን ተማሪዎች ገልጸዋል።

ተማሪዎች ከመጀመሪያው ቀን ጀምሮ  በዘራቸው ተከፋፍለው እንዲሰለጥኑ መደረጉን የከፋፍሎ መግዛት አንዱ ስትራቴጂያችሁ ነው በማለት ሲቃወሙ ቆይተዋል። ልማትን

በተመለከተ በቀረበው ሪፖርትር ደግሞ ተማሪዎች አገሪቱ ልትከፍለው በማትችለው እዳ ውስጥ መዘፈቋን በመግለጽ ሪፖርቱን ውድቅ አድርገዋል። የኢህአዴጉ አወያይ

ኢትዮጵያ እዳ መክፈል የምትችልበት ደረጃ ላይ በመድረሷ አበዳሪ አገሮች ብድር እንደሚሰጡዋትና ይህም የኢኮኖሚ እድገቱ ያመጣው መሆኑን ቢናገሩም፣ ተማሪዎች ግን

አበዳሪ አገሮች ለራሳቸው ጥቅም ሲሉ እንጅ በኢትዮጵያ ስለተደሰቱ ገንዘብ አያበድሩም፣ የአገሪቱ እዳ እየጨመረ ከሄደ ለአገራችን ህልውና አደገኛ ነው በማለት ተከራክረዋል።

“ጥቂት ባለሃብቶችና ባለስልጣኖች በበለጸጉት ሁኔታ የኢትዮጵያ ህዝብ እንደበለጸገ አድርጋችሁ የምታቀርቡት ትክክል አይደለም” በሚል ተማሪዎቹ ተናግረዋል።

ከቀደሙት ስርአት እንሻላለን በማለት የምትናገሩት አስቂኝ ነው ያሉት ተማሪዎች፣ ዜጎች እየተፋኑ፣ እየተገደሉና እየተሳደዱ መሆኑን በስፋት ገልጸዋል።

ተማሪዎች በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሰበብ መንግስት ከፍተኛ ሰብአዊ መብት የሚፈጽም በመሆኑ ” በአስቸኳይ ጊዜ ወቅት የዜጎች መብት የማይጣስ መሆኑ በግልጽ በህገ

መንግስቱ ላይ መቀመጥ አለበት” በማለት ሃሳብ ያቀረቡት ሲሆን፣ የመድረኩ መሪም በተማሪዎች ሀሳብ እንደሚስማሙ ገልጸዋል።

የሃረሪ ተማሪዎች በክልሉ ስላለው አስተዳደር ከፍተኛ ተቃውሞ ያሰሙ ሲሆን፣ መንግስት የበርካታ ነጋዴዎችን ድርጀቶች ሆን ብሎ በማቃጠሉ በቂ ካሳ ሊከፍላቸው ይገባል

በማለት ሀሳብ ሰጥተዋል።

በሀረሪ ክልል ተወልደው ያደጉ የዩኒቨርስቲ ምሩቃን ሀረሪኛ ቋንቋ አትችሉም በመባላቸው ስራ ለመቀጠር አለመቻላቸውን የገለጹት ተማሪዎች፣ ክልሉን ማስተዳደር ባለመቻላችሁ

ስልጣናችሁን ማስረከብ አለባችሁ የሚል ተቃውሞ አሰምተዋል። የክልሉ ባለስልጣናት ላነሳችሁት ጥያቄ ሌላ ጊዜ መልስ እንሰጣለን ቢሉም ተማሪዎች በር ዘግተው መልስ

ካልተሰጠን አትወጡም በሚል ባለስልጣኖች ሲያግቱ፣ ፌደራል ፖሊሶች ጣልቃ ገብተው ባለስልጣኖቹ እንዲወጡ ተደርጓል።

በድሬዳዋ ዩኒቨርስቲ ኢህአዴግ ተማሪዎች አባል እንዲሆኑ ጥያቄ አለማቅረቡን፣ የኢህአዴግ ደጋፊ የሆኑ ተማሪዎች ምንም አስተያየት ሳይሰጡ መውጣታቸውን ተማሪዎች ገልጸዋል።

በሀሮማያ ዩኒቨርስቲ የሚካሄደው የፖለቲካ ስልጠናም በተመሳሳይ መልኩ እየተካሄደ ሲሆን ዛሬ ወይም ነገ ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል። ይህ ዙር ሲጠናቀቅ ለመጀመሪያ አመትና

አዲስ ለሚገቡ ተማሪዎች ሌላ ዙር ውይይት እንደሚካሄድ የደረን መረጃ ያመለክታል።