በረሃቡ ምክንያት ከሰሜን ወሎ ተሰደው ደብረብርሃን ከተማ የሰፈሩት ዜጎች በሃይል ወደ ቀያቸው ተወሰዱ

የካቲት ፳፬ (ሃያ አራት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በደብርሃን ከተማ እና አካባቢዋ የነበሩትን ከሰሜን ወሎ ተሰደው በመምጣት በከተማዋ ውስጥ በመዘዋወር የእለት እንጀራቸውን ለማግኘት ሲጥሩ የነበሩ ስደተኞችን የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች‹‹ ማረፊያ አዘጋጅተናል››በማለት ከሰበሰቡና በአንድ ቦታ ካከማቹ በኋላ አርብ የካቲት18/2008 ዓም. ከ70 በላይ የሚሆኑ ተጎጂዎችን በአንድ አውቶብስ ከነልጆቻቸው በማሳፈር ወደ መጡበት መልሰዋቸዋል፡፡
ወደ አውቶቡስ በሚያስገቧቸው ሰዓት ‹‹የት ልትወስዱን ነው ?›› ብለው ሲጠይቁ የከተማዋ አመራሮች ‹‹እርዳታ ወደ ምታገኙበት ቦታ ››ቢሉም ተጎጂዎቹ ግን ‹‹ስንቃጠል ወደነበርንበት ቦታ ተመልሰን አንሄድም፣ በልጆቻችሁ ተውን!!›› በማለት ሲማጸኑ ተሰምተዋል፡፡
ምንም ርህራሄ ያላሳዩት የከተማዋ አመራሮች ግን ዜጎቹን በፖሊስ በማስገደድ በመኪና ጭነው ወስደዋቸዋል፡፡የሚሄዱበትን አቅጣጫ የተመለከቱት አብዛኛው ስደተኞች በአውቶብሱ መስኮት እስከ ግማሽ አካላቸው ወጥተው የከተማው ህዝብ እንዲያድናቸው በጩኸት ተማጽነዋል።‹‹ይህ ሌባ መንግስት ፣ እዛ ሲያስርበን ከርሞ አሁን ሊገለን ነው ፡፡›› እያሉ በብስጭት ሲናገሩ እንደነበር የአይን ምስክሮች ተናግረዋል፡፡
በአውቶብሱ ውስጥ በር ላይና ከሹፌሩ ጎን ፖሊስ ተመድቦ ጥበቃ ከማድረጉም በላይ በመንገድ ላይ ችግር ከፈጠሩ በማለት አንድ መኪና የፖሊስ ሰራዊት አውቶብሱን አጅቦ ሄዷል።
የከተማው አመራሮቹም ከቀናት በፊት በረሃቡ ምክንያት ለተጎዱ መርጃ በማለት ያሰባሰቡትን ገንዘብ ለመኪና ክራይ እንዳዋሉት ነዋሪዎች ተናግረዋል።