በላፍቶ የተፈናቀሉት አባወራዎች 30 000 ደረሱ

ህዳር 4 (አራት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በላፍቶ ክፍለከተማ ወረዳ 01 ቤታቸው የፈረሰባቸውና ለጎዳና የተዳረጉ አባወራዎች ቁጥር 30 000 መድረሱን የአካባቢው ሰዎች ለኢሳት ገለጡ።

ወደጠቅላይ ሚኒስትርና የአዲስ አበባ መስተዳድር ከንቲባ ጽፈት ቤት ተሰብስበው በመሄድ ጥያቄዎቻቸውን ለማቅረብ መሞከራቸውን የገለጹት የአካባቢው ነዋሪዎች ያገኙት መልስ በፖሊስ መደብደብና መታሰር መሆኑን ለኢሳት ሬዲዮ ተናግረዋል።

የአዲስ አበባ መሬት አስተዳደር ህገወጥ ናቸው ሲል ባለፈው ሳምንት ማፍረስ ከጀመራቸው ቤቶች ውስጥ 30 000 አባወራዎችን ያፈናቀለ ሲሆን ነዋሪዎቹ አቤቱታቸውን ለከንቲባው ቢያቀርቡም የተሰጣቸው ምላሽ እንደሌለ ገልጠዋል።

በአሁኑ ሰአት ህጻናትና አዛውንት ታማሚዎችና ሴቶች በሜዳላይ ፈሰው ጸሀይናስ ብርድ እየተፈራረቀባቸው መሆኑን የገለጹት ነዋሪዎች የሚመለከተው አካልና የአለም ማህበረሰብ ጩሀታቸውን እንዲሰማ ጥሪ አስተላልፈዋል።

በአካባቢው ላይ ተወልደው ማደጋቸውንና ክ 10 አመት በላይ ህገወጥ ተብሎ በፈረሰባቸው ቤት ውስጥ መኖራቸውን የገለጹት የአካባቢው ሰዎች ህጋዊ የሚያረጋቸውን መስፈርት አሞልተው የመብራት ክፍያ ለመንግስት ከፍለውና በመንግስት የጸደቀ የልማት ተግባር በማከናወን ላይ እያሉ ቤቶቹ እንደፈረሱባቸው ገልጸዋል።