በሀገረማርያም በተደረገ ስብሰባ ህዝቡ የመንግስትን የአፈና አገዛዝ ነቀፈ

ህዳር ፲፯ (አስራ  ሰባት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በቦረና ዞን በሀገረማሪያም ከተማ ህዳር 14 ቀን 2005 ዓም  “ከተማዋን ለማልማት” በሚል አጀንዳ  በተጠራ ስብሰባ ላይ ነው ህዝቡ የ21 አመታት የአፈና አገዛዝ በቃን በማለት የተናገረው።

የኢሳት ወኪል እንደዘገበው  የዞን እና የወረዳ ባለስልጣናት ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የተውጣጡ ከ500 በላይ ሰዎችን ሰብስበው የ2004 ዓም አፈጻጸም ግምገማንና የ2005 ዓም እቅድን  ይፋ አድርገዋል።

ባለስልጣናቱ ለ2005 ዓም ለከተማዋ ግንባታ ከተያዘው በጀት ውስጥ ነዋሪው 50 በመቶ የሚሆነውን ወጪ ይሸፍናል ተብሎ እንደሚጠበቅ መግለጻቸውን ተከትሎ በተሰጠው እድል ነው ህዝቡ ስሜቱን ሲገልጽ የዋለው።

ወኪላችን እንደሚለው  ነዋሪዎች ፣ ”  እንዳንናገር ታፍኑናላችሁ፣  21 አመታት ሙሉ ስታስፈራሩን ቆይታችሁዋል፣ እኛ ተለጉመን ያለን ህዝብ ነን ለምንድነው በማናምንበት ጉዳኢ ላይ አስተያየት እንድንሰጥ የምታስገድዱን።” እያሉ ይናገሩ ነበር።

የመንግስት ባለስልጣናቱ የአፈጻጸም ችግር እንደነበር በመማንና ችግሮችን ለማስተካካል እንደሚሰሩ በመግለጽ ህዝቡን ለማግባባት ሞክረው ነበር። ይሁን እንጅ ህዝቡ ” ለ21 አመታት ምንም የሰራችሁት ነገር የለም ፣ መልካም አስተዳዳር ፣ ዲሞክራሲያዊ አስተዳዳር በሌለበትና ሰብአዊ መብቶች በማይከበሩበት ሁኔታ ምንም ልማት ሊኖር አይችልም። እዚህ ቦታ ላይ ራሳችሁን ትሾማላችሁ፣ ራሳችሁን ታነሳላችሁ፣ ህዝቡ በስልጣኑ ተጠቅሞ የሚያስቀምጠው፣ የሚያወርደው ሰው የለም፣ ስራችሁን አናይም ፣ የምናየው ነገር ቢኖር ህዝቡን ስታስፈራሩ ብቻ ነው” የሚል መልስ ሰጥቷል።

ስብሰባውም በውዝግብ መጠናቀቁ ታውቋል።

በተመሳሳይ ዜና ደግሞ በሀረሪ ክልል የሚገኙ የግብርና ባለሙያዎችን ለመገምገም በተጠራ ስብሰባ ላይ ውዝግብ ተፈጥሮ እንደነበር በስብሰባው ላይ የተሳተፉ ባለሙያዎች ለኢሳት ተናግረዋል።

ከህዳር 6 እስከ 12 አቶ ሀምዛ በሚባሉት የሀረሪ የግብርና ቢሮ ሀላፊ ሰብሳቢነት በተጠራ ስብሰባ ላይ የዲኤ ሰራተኞች፣ የቢሮ አመራሮች፣ ኤክስፐርቶችና የስራ ሂደቶች ተሳትፈዋል፡፡ የግምገማው ርእሶች  ”  የልማት ሰራዊት ግንባታን በሙሉ እምነት ተቀብሎ ከማደራጀትና ከመምራት አንጻር ያለበት ሁኔታ፣ ምርጥ ተሞክሮ መቀመር እና ማስፋፋት ፣ ሶስቱን የልማት ሀይሎች አቀናጅቶ መምራት፣ እንዲሁም የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከትን መታገል”  የሚሉት ነበሩ።

አቶ ሀምዛ አሁን የምንገመግማችሁ ከአመለካት፣ ከክህሎት እና ከግብአት አንጻር ነው” በማለት ካተናገሩ በሁዋላ፣ ” እኔ ክልል ላይ ስገመገም አልሰራሁም ብየ ነው የመጣሁትና እናንተም አልሰራንም ብላችሁ ተናገሩ።” በማለት  ባለሙያዎችን ሲማጸኑ ውለዋል።

ሰራተኞችም ” እኛ የሰራነውንም ያልሰራነውንም እስከ ምክንያቱ  እንገልጻለን።” በማለት አስተያየት ሲሰጡ ባለስልጣኑ በማቋረጥ ”  ያልሰራችሁበትን ምክንያት መስማት አልፈልግም፣ አልሰራሁም ብቻ በሉ” በማለት አስጠንቅቀዋል። ባለስልጣኑ የስብሰባው ዋና አላማ ገበሬውን አንድ ለአምስት ለማደራጀት መሆኑን በማስታወስ ሰራተኞች ትኩረት ሰጥተው ገበሬውን እንዲያደራጁ መመሪያም አስተላልፈዋል።

ሰራተኞች ” የአንድ ለአምስት አደረጃጃት ግቡን አልመታም፣ ገበሬው ለመደራጀት ፍላጎት የለውም፣ ህብረተሰቡ አንድ ለአምስት አደረጃጃት ለፖለቲካ መጠቀሚያ ተብሎ የተዘጋጀ ነው የሚል ትችት በማቅረቡ ሳይፈልጉ ያደራጀናቸው ገበሬዎች አንፈልግም እያሉ ነው።” በማለት ተናግረዋል።

አብዱልመጂድ  የተባለ የተፈጥሮ ሀብትና ሴፍቲኔት ኤክስፐርት ” ያልረሳሁበትን ምክንያት መግለጽ አለብኝ፣ ይህን ካልገለጽኩኝ አልገመገምም” የሚል ጠንካራ አቋም በማንጸባረቁ፣ የቢሮ ሀላፊው ” አርፈህ ማትቀመጥ ከሆነ ከዚህ ትባረራለህ” በማለት እንዳስጠነቀቁት ስብሰባውን የተካፈሉት ባለሙያዎች ገልጸዋል።

አብዱልመጅድ ጥያቄ መጠየቁን ባለማቆሙ፣ የቢሮው ሀላፊው መድረኩ ላይ ከስራ አባረውታል።  ሌሎች አንጋፋ ሰራተኞች ” የሶስት ልጆች አባት ነው” በሚል ባለስልጣኑን ቆመው በመለመን ወደ ስራው እንዲመለስ ማድረጋቸውም ታውቋል።

የግብርና ሰራተኞች በሚደርስባቸው የሰብአዊ መብቶች ጥሰት መማረራቸውንም ገልጸዋል