የቆዳ እንዱስትሪው በጨው እጥረት አደጋ ላይ ነው ተባለ

ህዳር ፲፯ (አስራ  ሰባት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በዚህ ዓመት ከኤክስፖርት 200 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስገባ እቅድ የተያዘለት  የቆዳ ኢንደስትሪ በጨው አቅርቦት እና  በተለያዩ ግብዓቶች እጥረት አጣብቂኝ ውስጥ መግባቱን የዘገበው ሪፖርተር ነው

 

የ ቆዳ ኢንዱስትሪዎች ማህበር በ አምስት ወር 150 ሺህ ኩንታል ቸው ሊደርሰን ሲገባ፤ያገኘነው ግን አምስት ሺህ ኩንታል ብቻ ነው አለ።

የአፋር ክልል በበኩሉ፦-<< ምንም ዓይነት  የ አቅርቦት ችግር አልተፈጠረም> ይላል።

 

የኢትዮጵያ ቆዳ ኢንዱስትሪዎች ማኅበርና -ግብዓት አቅራቢው የኢትዮጵያ ቆዳ ልማት አክሲዮን ማኅበር  በጋራ እንዳስታወቁት፣ በከፍተኛ የጨው አቅርቦት ችግር ውስጥ የሚገኙት ኢንዱስትሪዎች ጥሬ ቆዳ እየተበላሸባቸው ከመቸገራቸውም በላይ፣ በጥራት ችግር ምክንያት የቆዳ ምርታቸው ተገቢውን ዋጋ ማግኘት ተስኖታል፡፡
የቆዳ ኢንዱስትሪዎች ከመላ አገሪቱ የሚሰበስቡት ቆዳ- በጨው ታሽቶና ደርቆ የሚዘጋጅ ሲሆን፣ ለምርት ሥራም ሆነ ቆዳና ሌጦ ሳይበላሽ ለማቆየት በዓመት እስከ 350 ሺሕ ኩንታል አዮዲን ያልተቀላቀለበት ጨው ያስፈልጋቸዋል፡፡

ይሁንና  ዘንድሮ ኢንደስትሪዎቹ  የሚያስፈልጋቸውን ጨው  ጨርሶ  ለማለት በሚያስደፍር አኳሁዋን  ሊያገኙ አለመቻላቸው ተገልጿል።

 

ባለፉት አምስት ወራት ከሚያስፈልጋቸው 150 ሺሕ ኩንታል ውስጥ ማግኘት የቻሉት አምስት ሺሕ ብቻ እንደሆነ  ነው  የኢትዮጵያ ቆዳ ኢንዱስትሪዎች ማኅበር ዋና ጸሐፊ አቶ አብዲሳ አዱኛ የተበናገሩት፡፡

በ አፋር ክልል ከአፍዴራ ጨው አምራቾች ድጋፍ ሰጭ ማኅበር  ላለፉት ስድስት ዓመታት የጨው አቅራቢ ሆኖ ይሠራ የነበረው አንድ ግለሰብ ብቻ መሆኑን ጠቀሱት አቶ አብዲሳ፣ በአሁኑ ጊዜ ቁጥራቸው ሦስት እንዲደርስ ቢደረግም የአቅርቦቱ ችግር ተባብሶ እንደቀጠለ ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ቆዳ ልማት አክሲዮን ማኅበር ዋና ሥራ አስኪያጁ አቶ ይሄይስ መርሻ በበኩላቸው፣ የፌደራል መንግሥት -አንዴ በንግድ ሚኒስቴር ሚኒስቴር ሌላ ጊዜ በኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድኃኒትና ጤና እንክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለሥልጣን በኩል፦ ኢንዱስትሪዎቹ የሚያስፈልጋቸው የጨው መጠን በዝርዝር ቢጽፍም፣ የሚፈለገው የጨው መጠን ባለመገኘቱ ብቻ ሳይሆን የሚቀርበውም ጥራት የጎደለው አፈራማ ጨው በመሆኑ፣ በቆዳና በሌጦ ላይ ብክለት እያስከተለ አገሪቱ ማግኘት የሚገባትን የውጭ ምንዛሪ እያሳጣት ይገኛል ብለዋል፡፡

አቶ ይሄይስ ፤የጨው ምርቱ በገፍ እያለ ሆን ተብሎና ሞኖፖልን በመጠቀም የጨው እጥረቱ በቆዳ ኢንዱስትሪዎቹ ላይ እንዲከሰት ተደርጓል ባይ ናቸው።  በዚህም ሳበአገሪቱ ከዚህ ቀደም የነበራት 30 በመቶ ጥራት ያለው ጥሩ ቆዳ- በአሁኑ ጊዜ ወደ 10 በመቶ መውረዱን ተናግረዋል፡፡

ከአፋር ክልል የሚመጣውን ጨው በዛ ከተባለ በኩንታል እስከ 160 ብር ፋብሪካዎቹ ለመግዛት ዝግጁ ቢሆኑም፣ የሚጠየቁት ዋጋ እስከ 300 ብር ማሻቀቡን ተናገሩት አቶ ይሄይስ፤ አዮዲን እንተቀላቀለበት ጨው እኩል ዋጋ መጠየቁ- የቆዳና ሌጦ ማምረቻ ወጪን እንደሚያንረው አብራርተዋል።

ለጨው ፍጆታ ብቻ እስከ 12 ሚሊዮን ብር በማውጣት ለማምረት መገደድ በውጭ ገበያ ተፎካካሪ እንደማያደርግ ም ገልጸዋል።

እንደ አቶ ይሄይስ ገላፃ እንደ ህንድ፣ ፓኪስታንና የመን የመሳሰሉ አገሮች ለአንድ ኩንታል ጨው በአማካይ ሦስት ዶላር ሲያወጡጸ የኢትዮጵያ ቆዳ ፋብሪካዎች ወጪ  እስከ ስምንት ዶላር ይደርሳል።

ይህ የሆነውም ዋጋው የናረው ጨው በመኖሩ ሳይሆን አቅርቦቱ በኮታ እንዲሆን በመደረጉ ነው ይላሉ  ሥራ አስኪያጁ።

 

ስለ ጉዳዩ የተጠየቁት የአፋር ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ኢስማኤል አሊሴሮ፣ የጨው አቅርቦት እጥረት የለም  በማለት ኢንዱስትሪዎቹ  ያቀረቡትን ጥያቄ ውድቅ አድርገዋል፡፡

በየቀኑም ከሚጫነው 30 መኪና ጨው በተጨማሪ በወር 360 ኩንታል እንደሚሰራጭ የጠቀሱት ፕሬዚዳንቱ፣ <<የአቅርቦት ችግር ፈጽሞ ሊኖር አይችልም >>በማለት አስተባብለዋል፡፡

አቶ እስማኤል እንዳሉት ከክልሉ ጋር እየሰሩ ያሉት አቅራቢዎች በኩንታል 80 ብር እየተቀበሉ ነው የሚያከፋፍሉት።  የቆዳ አክስዮን ማህበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ይሄይስ እንደሚሉት ደግሞ  ፋብሪካዎች በኩንታል  160 ብር ለመግዛት ዝግጁ ቢሆኑም ዋጋው ወደ 300 ብር አሻቅቧል።

በኩንታል  80 ብር የተረከቡትን ጨው- በ300 ብር የሚያከፋፍኩት እነማን ናቸው? የሚለው በተብራራ መልክ አልተቀመጠም።

<<ችግሮች ካሉ ወደ እኛ መጥተው እንነጋገር >>ያሉት አቶ ኢስማኤል፣ በጨው አቅርቦቱ መሀል እየገቡ ሊያስቸግሩ የሚችሉ አካላት ሊኖሩ እንደሚችሉም ግን  ሳይጠቁሙ አላለፉም፡፡

ይሁንና በአቅርቡቱ መሀል ጣልቃ እየገቡ ችግር እየፈጠሩ ናቸው ያሏቸው አካላት እነማን እንደሆኑ ፕሬዚዳንቱ በግልጽ አልተናገሩም።