ሱዳንና ኢትዮጵያ በድንበር አካባቢ የጋራ ጥምር ሃይል ለማቋቋም ተስማሙ

የካቲት ፳፩ (ሃያ አንድ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የሱዳን የመከላከያ ሚኒስትር አብዱል ራሂም ሙሀመድ እንዳሉት ሁለቱ አገራት ከየመከላከያ ሰራዊታቸው የተውጣጡ ጥምር ሃይል በማቋቋም በድንበሮች ላይ አሰሳ ማድረግ ይጀምራሉ።

ሚኒስትሩ በሁለቱ መንግስታት መካከል የሚደረገው ተከታታይ ውይይት እዚህ ውሳኔ ላይ እንዲደርሱ አድርጓቸዋል። ስምምነቱን  በኢትዮጵያ በኩል  የመከላከያ ሚኒሰትር ሲራጅ ፈርጌሳ ፈርመዋል።

የኢትዮጵያ መንግስት በርካታ የአገሪቱ ዜጎች የትጥቅ ትግል ለማድረግ የሚንቀሳቀሱት ተቃዋሚዎችን ለመቀላቀል በሱዳን በኩል እንደሚያቋርጡ በቂ መረጃ አለው። የእነዚህ ተቃዋሚ ሃይሎች ጉልበት እየተጠናከ መምጣት ያሰጋው መንግስት ከሱዳን ጋር ያለውን ግንኙነት በማጠንከር የተቃዋሚዎችን የመንቀሳቀሻ ቦታዎችን ለመዝጋት ማለሙን ጉዳዩን በቅርብ የሚከታተሉ ሰዎች ይገልጻሉ። የሱዳንን መንግስት ድጋፍ ለማግኘት ሰፊ የሆነ የአገሪቱን መሬት አሳልፎ መስጠቱን እነዚህ ወገኖች ያስረዳሉ።