ህወሀት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርን ቦታ ሊወስድ መዘጋጀቱ ታወቀ

ጥቅምት ፫ (ሦስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የአቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ እና የአቶ ደመቀ መኮንን ጠቅላይ እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ሆኖ መሾም፣ በኢህአዴግ አጋር ድርጅቶች ውስጥ በተለይም በኦሮሞ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ድርጅት ተቀባይነት ማጣቱ እየተነገረ ባለበት በዚህ ወቅት፣ የሀይለማርያም መንግስት ኦህዴድን የሚያስከፋ በተወሰነ መጠን የህወሀትን ተቃውሞ ሊያረግብ የሚችል እርምጃ ለመውሰድ መዘጋጀቱ ታውቋል።

በመንግስት የስልጣን ተዋረድ ከጠቅላይ ሚኒስትርነት ቀጥሎ የተሻለ ቦታ ተደርጎ የሚታየውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት ቦታ የህወሀቱ ነባር ታጋይ እና የአቶ መለስ ዜናዊ የቅርብ ጓደኛ በመሆን እስከ መጨረሻው በማስታመም ከጎናቸው ያልተለዩት አቶ ብርሀነ ገብረ ክርስቶስ ይወስዱታል ተብሎ እየተጠበቀ ነው። አቶ ብርሀነ አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ የጠቅላይ ሚኒሰትርነቱን ቦታ ከተረከቡ ጀምሮ፣ ተጠባባቂ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በመሆን እየሰሩ ይገኛሉ።

 

አቶ መለስ ዜናዊ በህመም ምክንያት ወደ ስራ ገበታቸው እንደማይመለሱ ከታወቀበት ጊዜ ጀምሮ አቶ ብርሀኔ ገብረክርስቶስ የአቶ መለስን ቦታ ይተካሉ እየተባለ በስፋት ይነገር ነበር። ይሁን እንጅ የመንግስቱን አደራ ከአቶ መለስ የተረከቡት አቶ በረከት ስምኦን፣ ህወሀት ተመልሶ ወደ ጠቅላይ ሚኒሰትርነት ቦታ እንዳይመጣ በያዙት አቋም፣ አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝን ለማስመረጥ ችለዋል።

በአቶ ሀይለማርያም መሾም ያልተደሰቱት ወ/ሮ አዜብ መስፍን ወደ ትግራይ ክልል ተመልሰው የአቶ መለስን ታማኞች  በማሰባሰብ እንዲሁም የጠቅላይ ሚኒስትሩን ሹመት የተቃወሙትን የኦህዴድ አመራር አካላት በማስተባበር በስልጣን ክፍፍሉ ውስጥ አለሁ ለማለት እየታገሉ መሆኑ ታውቋል። እንደዜና ምንጮቻችን ከሆነ በኦህዴድ ውስጥ ለተፈጠረው መተራመስ የወ/ሮ አዜብ መስፍን ሚና ከፍተኛ ነበር።

ወ/ሮ አዜብ ከአቶ ሀይለማርያም ጋር የነበራቸው አለመግባባት የቆየ እንደነበር መረጃዎች ያሳያሉ። አቶ በረከት በእጩነት ካቀረቡዋቸው አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ እና አቶ ደመቀ መኮንን ሌላ፣ ታማኛቸው የሆኑትን የገንዘብ ሚኒስትሩን አቶ ሶፍያን አህመድን በእጩነት በማቅረብ፣ ለማስመረጥ ሞክረው ሳይሳካላቸው ቀርቷል። ወ/ሮ አዜብ አቶ ሶፍያን አህመድ ሊመረጡ እንደማይችሉ እያወቁ ጥቆማውን ያካሄዱት ከኦህዴድ ጎን መሰለፋቸውን ለማሳየት እና የአቶ ሀይለማርያምን ሹመት ለመቀበል አለመፈለጋቸውን ለማሳየት ነበር። የአቶ ሶፍያን አለመሾም ያበሳጫው አንዳንድ የኦህዴድ ከፍተኛ አመራሮች ፣ ከወ/ሮ አዜብ መስፍን ጋር በመሆን ውስጥ ለውስጥ የሚያደርጉትን ትግል እንደቀጠሉ ይነገራል።

 

አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ የውጭ ጉዳይ ሚኒሰትርነት ቦታ ለኦህዴድ በመስጠት ፣ የድርጅቱን ከፍተኛ አመራሮች ለማረጋጋት ይጥራሉ ተብሎ ቢጠበቅም ፣ በህወሀት በኩል ያለው ፈቃደኝነት አነስተኛ ሆኖ በመታየቱ ሳይቻል ቀርቷል። ወ/ሮ አዜብ መስፍን በአቶ ሀይለማርያም ካቤኔ ውስጥ ይካተቱ አይካተቱ የታወቀ ነገር የለም።

በሌላ ዜና ደግሞ 4ኛው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 3ኛ አመት የስራ ዘመን 2ኛ መደበኛ ስብሰባ ጥቅምት ስድስት ፣ 2005 ዓም የሚካሄድ ሲሆን በፕሬዚዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ የተደረገውን የመክፈቻ ንግግር አስመልክቶ በበቀረበው የማሻሻ ሞሽን ላይ የመንግስትን አቋም ያጸድቃል። አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ በፓርላማው ተገኝተው ከፓርላማ አባላት የሚቀርብላቸውን ጥያቄ በመመለስ የመንግስታቸውን አቋም ግልጽ ያደርጋሉ ተብሎአል። አዲሱን ካቢኔያቸውን ይፋ ያድርጉ አያድርጉ እስካሁን የታወቀ ነገር የለም።