አዲሱ ፓርቲ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ በሚል ስያሜውን አጸደቀ

(ኢሳት ዲሲ–ግንቦት 1/2011) የሰባት የፖለቲካ ሃይሎች ውህደት የሆነው አዲሱ ፓርቲ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ በሚል ስያሜውን አጸደቀ።

መስራች ጉባዔውን ዛሬ በአዲስ አበባ የጀመረው አዲሱ ፓርቲ ከተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ከ300 በላይ ወረዳዎች በተወከሉ የመስራች ጉባዔ አባላት መተዳደሪያ ደንብ፣ አወቃቀር እና አርማ ላይ ውሳኔ በመስጠት እየተካሄደ መሆኑን የመስራች ጉባዔው አስተባባሪዎች ለኢሳት ገልጸዋል።

በድምጽ የሚሳተፉ 1200 የጉባዔ አባላት የአዲሱ ፓርቲ አመራሮችን ይመርጣሉ ተብሎ ይጠበቃል።

ፓርቲው በማህበራዊ ፍትህ ላይ መሰረት በማድረግ የዜግነት ፖለቲካን እንደሚያራምድም በመስራች ጉባዔው ላይ ተገልጿል።

አቶ አንዱዓለም አራጌ የመስራች ኮሚቴ አባል ጉባዔው ታሪካዊ ነው ሲሉ ገልጸውታል።