በአማራ ክልል ትጥቅ የማስፈታቱ ሙከራ አሁንም አልተሳካም

( ኢሳት ዜና -ሃምሌ 3 , 2009 )

በአማራ ክልል አርሶ አደሩን ትጥቅ ለማስፈታት ከሚሊሻ ሃላፊዎችና ከፖሊስ ጋር በተቀናጀ መልኩ የተጀመረው ዘመቻ ቢጠናከርም አሁንም አለመሳሳቱ ተነገረ ።

በህዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ / ህውሃት / የሚመራው ወታደራዊ እዝ / ኮማንድ ፖስት / በመሳሪያ ምዝገባና በግብር ስም የጠራው ስብሰባ መጨናገፉም ተገልጿል ።

በጎጃምና በጎንደር ድንገተኛ የቤት ለቤት ፍተሻ እየተካሄደ መሆኑንም የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል ።  

 በጎጃም ሸበል በረንታ ወረዳ ይጠሃና ቀበሌ የሚኖሩ አርሶአደሮች በሰሜን ሸዋ ደራ እንዲሁም ደቡብ ወሎ ወግዲ የቤት ለቤት ፍተሻ ለማካሄድ ታቅዶ መክሸፉን የአካባቢው ነዋሪዎች ይናገራሉ ። በመሳሪያ ምዝገባና በግብር ስም የተጠራው ስብሰባም ከሚሊሻዎችና ከፖሊስ አካላት ሳይቀር ተቃውሞ እየገጠመው መሆኑን ለማውቅ ተችሏል ። የመሳሪያ ገፈፋውን የተቃወሙ የሚሊሻና የፖሊስ አባላት ከጸረ ሰላም ሃይሎች ጋር ትሰራላቹ በሚል ችግር እየደረሰባቸው እነደሆነም ነው የተነገረው ።ከዚሁ ጋር በተያያዘ በወረዳው ጣታና ጢሮ አካባቢዎች በዛምበራ ጫካ የሚኖሩ አርሶአደሮችን ለጦር መሳሪያችሁ ግብር ክፈሉ በማለት ለመደለል ያደረጉት ሙከራም እንዳልተሳካ የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል ።

በሸበል በረንታ 19 ቀበሌዎች ያሉ ካድሬዎችን በየእድ ውሃ ከተማ ሰብስበው ገበሬውን ትጥቅ ለማስፈታት እንዴት ይቻላል ሲሉ ምክክር ቢደረግም ስምምነት ላይ መድረስ እንዳልተቻለ ተነገሯል ። ካድሬዎቹ ገበሬው ብሶት ስላለበት ባትነካኩት ይሻላል ማለታቸውም ተገልጿል ። በሰሜን ጎንደር አንቃሽ ወረዳ በደቡብ ጎንደር ደግሞ እብናት በጎጃም ጃዊ ወረዳ የጀመሩት በሃይል ትጥቅ የማስፈታት ዘመቻም አለመሳካቱም ታውቋል ።