ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ የባለ አደራ ኮሚቴ በሚል የሚስተዋለው እንቅስቃሴ  ሕገ ወጥ ነው አሉ

 (ኢሳት ዲሲ–መጋቢት 25/2011) ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ አዲስ አበባን በተመለከተ የባለ አደራ ኮሚቴ በሚል የሚስተዋለው እንቅስቃሴ  ሕገ ወጥ ነው ሲሉ አስጠነቀቁ።

ዶክተር አብይ  አህመድ የፖለቲካ በሽታና ችግር በልሂቃን፣ በአክቲቪስቶች እና በፖለተከኞች ላይ የሚስተዋል ችግር መሆኑንም አዲስ ወግ በተሰኘው የውይይት መድረክ  ላይ ባደረጉት ንግግር  አንስተዋል።

በኢትዮጵያ በምርጫ በሚካሄድ ፉክክር ስልጣናቸውን ለመልቀቅ ፈቃደኝነታቸውን የገለጹት ጠቅላይ ሚንስትር አብይ አህመድ በባላደራ ስም በሚደርግ አይነት እንቅስቃሴ  ግን ግልጽ ጦርነት እንከፍታለን ብለዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ከወቅታዊው የፖለቲካ ሁኔታ ጋር በተያያዘ አዲስ ወግ በተሰኘው የውይይት መድረክ  ላይ ባደረጉት ንግግር በአሁኑ የኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ የሰከነ ውይይት እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።

የፖለቲካ በሽታና ችግር በልሂቃን፣ በአክቲቪስቶች እና በፖለተከኞች ላይ የሚስተዋል መሆኑንም በንግግራቸው በመግለጽ።

ልግመኝነት፣ ህሊና ቢስነት እና አቅላይነት እንዲሁም ከሌላ አካል ወደ እኛ የሚገቡ አስተሳሰቦች ለፖለቲካው መበላሸት ምክንያት ናቸው ሲሉ ዶክተር አብይ  አህመድ  ገልጸዋል።

ፖለቲከኞችም ጊዜን በማሻገርና ትናንት ከዛሬ ጋር በማዛመድ ትውልድ መቅረጽ ይገባቸዋል ነው ያሉት።

በኢትዮጵያውያን የበዛ ጥላቻ፣ በቀል እና አለመግባባት አለ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ ብዙ ችግር ተሸክሞ መጓዝ ስለማይቻል ይህን ማራገፍና መቅረፍ ተገቢ መሆኑን በአጽንኦት ተናግረዋል።

በሃገሪቱ የፖለቲካ ዋልታ ረገጥነት እንደሚስተዋል ጠቅሰውም፥ ኢትዮጵያ እንድትቆይና እንዳትፈርስ የሚፈልግ ዜጋም ከአፍራሽ ሃሳቦች መራቅና በእነዚህ ሃሳቦች ከመዳከር መራቅ አለበት ሲሉ ነው የገለጹት።

ጠቅላይ ሚንስትር አብይ አህመድ አዲስ አበባን በተመለከተ የባለ አደራ ኮሚቴ በሚል የሚስተዋለው እንቅስቃሴ  ሕገ ወጥ ነው ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

በኢትዮጵያ በምርጫ በሚካሄድ ፉክክር ስልጣናቸውን ለመልቀቅ ፈቃደኝነታቸውን የገለጹት ጠቅላይ ሚንስትር አብይ አህመድ በባላደራ ስም በሚደርግ አይነት እንቅስቃሴ  ግን ግልጽ ጦርነት እንከፍታለን ብለዋል።

ከቀጣዩ ሃገራዊ ምርጫ ጋር በተያያዘ ምርጫው በዴሞክራሲያዊ መንገድ እንዲካሄድ መስራት እንደሚያስፈልግ ጠቅሰው፥ በምርጫው ተፎካካሪ ፓርቲ ቢያሸንፍ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ስልጣን እናስረክባለን ብለዋል።

በሃገሪቱ የሚስተዋለው ሁኔታ የመስከን ጊዜ ላይ እስከሚደርስም የሚታየው ፅንፈኝነትና ዋልታ ረገጥነት ለጥቂት ጊዜ እንደሚቀጥልም ነው የተናገሩት።

በሃገሪቱ በማህበራዊ የትስስር ገጽ በተለይም በፌስ ቡክ አጠቃቀም ዙሪያ ችግር እንዳለም ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመደ ገልጸዋል።

ይህን ለማስተካከል የሚያግዝ ህግ እየተዘጋጀና ከፌስ ቡክ ኩባንያ ጋር በጉዳዩ ዙሪያ ንግግር እየተደረገ መሆኑንም አስታውቀዋል።