ደርግ ከ 26 ኣመት በፊት  በትግራይ-በሀውዜን ላይ በፈጸመው ጭፍጨፋ የእስራ ዔል እጅ አለበት ሲሉ የህወሀት መስራች የሆኑት አቶ ስብሀት ነጋ ተናገሩ።

ታኀሳስ ፳፬(ሃያ አራት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ሰንደቅ ጋዜጣ እንደዘገበው፣የቀድሞው የህወሀት ሊቀመንበር አቶ ስብሀት ነጋ ይህን ያሉት የህወሀትን 40ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ ሰሞኑን ወደ ትግራይ ለተንቀሳቅቀሱት  ጎብኝዎች የደርግ 604ኛ ኮር የተደመሰሰበትን ወታደራዊ ሳይንስ አስመልክቶ  በሽሬ ከተማ በተሰናዳ መድረክ ላይ ባደረጉት ገለጻ ነው።

“የቀዝቃዘውን ጦርነት ማክተም ተክትሎ ታላቋ ሶቪየት ህብረት መፈራረስ ጀመረች ያሉት አቶ ስብሀት፤ክስተቱን ተከትሎ ሲቪየት  ከኢትዮጵያ እየወጣች በመምጣቷ በእሷ እግር የተተካው የሩሲያ ፌዴሬሽን ለደርግ ይለግስ የነበረውን እርዳታ ማቋረጡን ተናግረዋል።

አቶ ስብሀት አክለውም፦”ይህን ዓለማቀፍ ዳይናሚዝም ተከትሎ አሜሪካ መራሹ የምእራቡ ዓለም እና እስራኤል የደርግ ወዳጅ ሆኑ”ብለዋል።

የደርግን መውደቅ ተከትሎ ሊፈጠር የሚችለውን የጂኦ ፖለቲካል ሀይል አሰላለፍ በመፍራት እስራዔልና የምእራቡ ዓለም  ደርግን ወዳጅ አድርገው በኛ የግል እንቅስቃሴ ላይ አሉታዊ  እርምጃዎች መውሰድ ጀመሩ”ሲሉም  አቶ ስብሀት ተናግረዋል።

በወቅቱ ህወሀት ወታደራዊ አቅሙ እየጠነከረ በመምጣቱ አሜሪካና እስራዔል ድንጋጤ ውስጥ ገቡ ያሉት አቶ ስብሀት፤ በወቅቱ  ደርግን ለማትረፍ ያልሞከረ የምእራብ ሀገር የለም፤ሁሉም የሚችለውን አድርጓል፣ አሜሪካ ለማደራደር ስትሞክር እስራዔል  ግን የተለዬ ሚና ወሰደች”ብለዋል።

አሜሪካ አንድ ጊዜ ወደ ሮማ ሌላ ጊዜ ወደ ለንደን ጠራችን ያሉት የቀድሞው የህወሀት ሊቀመንበር፤”ሮማ ላይ ጂሚ ካርተር ሲያስጠራን የደርግ ልኡካን እናንተ ስለኢትዮጵያ ምን ያገባችሁዋል አሉን፤ወደ ለንደን ስንሄድ ግን ሁሉን ነገር ስለጨረስን ደርግን ጥለን ነበር”ብለዋል።

“እስራዔል ግን ወደ ሮም ከመሄዳችን በፊት ደርግን ማስታጠቅ ጀምራ ነበር”ያሉት አቶ ስብሀት፤ “ደርግም የታጠቀውን ክላስተር ቦንብ ጁን 22፣ 1988  ዘውዜን በገበያ ቀን ህዝቡ ላይ አዘነበው ብለዋል። በጥቃቱ ከ2 ሺ 500 በላይ ህዝብ ማለቁን የጠቀሱት አቶ ስብሀት “ይህ ሁሉ የህዝብ እልቂት በ እስራኤል አስታጣቂነት የተፈጸመ ነበር”ብለዋል።

መንግስት በሃውዜና ጭፍጨፋ የእስራኤል እጅ አለበት ካለ፣ እስራኤልን እስካሁን በይፋ በአለማቀፍ ፍርድ ቤት ለምን ለመክሰስ እንዳልደፈረ ግልጽ አይደለም።

ነባሩን የህወሀት አመራር አቶ ገብረመድህ አርአያን ጨምሮ በርካታ ድርጅቱን የከዱ ሰዎች ፤ ለዓለማቀፉ ህብረተሰብ የድጋፍ  መጠየቂያ እንዲሆን በህወሀት  ሰዎች በከፍተኛ ዝግጅት በዘመናዊ ካሜራ ለተቀረጸው   የሀውዜን ጭፍጨፋ ዋነኛው ተጠያቂ፦ የህወሀት አመራሮች እንደሆኑ በተደጋጋሚ ሲከሱ ቆይተዋል።

ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ ክስ ተመስርቶባቸው የነበሩትም የቀድሞው መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣን አቶ ለገሰ አስፋው ከ 20 ዓመት እስራት በሁዋል በምህረት መፈታታቸው ይታወሳል።

ጉዳዩን በተመለከተ በኢትዮጵያ-የ እስራዔል አምባሳደርን በማነጋገር የሚሰጡንን ምላሽ ለማቅረብ ጥረት እናደርጋለን።