ዮዌሪ ሙሴቬኒ ዶናልድ ትራምፕን አደነቁ

(ኢሳት ዲሲ–ጥር 16/2010)

አሜሪካ በታሪኳ ካገኘቻቸው ምርጥ ፕሬዝዳንቶች አንዱ ዶናልድ ትራምፕ ናቸው ሲሉ የዩጋንዳው መሪ ዮዌሪ ሙሴቬኒ ገለጹ።

ዶናልድ ትራምፕ አፍሪካን በተመለከተ በግልጽ በመናገራቸው ወድጄያቸዋለሁ በማለት ከቅሬታና ተቃውሞ ይልቅ አድናቆት ቸረዋቸዋል።

ዶናልድ ትራምፕ በኢሚግሬሽን ጉዳይ ላይ በዚህ ወር መጀመሪያ በኋይት ሃውስ በተደረገ ስብሰባ የአፍሪካ ሀገራትን ውዳቂ ሲሉ መጥራታቸው ይታወሳል።

አፍሪካን በተመለከተ ዶናልድ ትራምፕ በግልጽ በመናገራቸው ወድጄያቸዋለሁ በማለት ዮዌሪ ሙሴቬኒ አስተያየታቸውን የሰነዘሩት በዩጋንዳ ርዕሰ መዲና ካምፓላ በተካሄደው የምስራቅ አፍሪካ ሕግ አውጪዎች ስብሰባ ላይ ነው ይላል አልጀዚራ በዘገባው።

አሜሪካ በታሪኳ ከገጠሟት ምርጥ ፕሬዝዳንቶች አንዱ ነው በማለት በአፍሪካ መዲና ለአፍሪካውያን በተዘጋጀው ስብሰባ ላይ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕን ያወደሱት ዮዌሪ ሙሴቬኒ በፕሬዝዳንቱ ንግግር ከመናደድ ይልቅ አፍሪካውያን ችግራቸውን እንዲፈቱና ጠንክረው እንዲቆሙ አሳስበዋል።

ደካማ ከሆናችሁ በአለም ላይ ተገቢ ስፍራ አይኖራችሁም ደካማነታችን ደግሞ የአፍሪካውያን የራሳችን ጥፋት እንጂ የሌላ የማንም አይደለም በማለት በዶናልድ ትራምፕ አትማረሩ ወይንም አታሳቡ የሚል መልዕክት አስተላልፈዋል።

ለሶስት አስርት አመታት በዩጋንዳ የመሪነት ስፍራ ላይ የተቀመጡት የዌሪ ሙሴቬኒ በምዕራባውያን አዲስ አመት መጀመሪያ ለዩጋንዳ ሕዝብ ባደረጉት ንግግርም የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕን ሀቀኛ ሰው ሲሉም ማወደሳቸው ተመልክቷል።

የአሜሪካው መሪ ዶናልድ ትራምፕ በወሩ መጀመሪያ ተጨማሪ የአፍሪካ ስደተኞች በተለየ ሁኔታ አሜሪካ መግባት በሚችሉበት ሁኔታ ላይ ሃሳብ ሲቀርብላቸው ከነዚህ ውዳቂ ሀገራት የሚመጡ ሰዎች ምን ያደርጉልናል የሚል ምላሽ መስጠታቸው ይታወሳል።

ባይሆን ኖርዌይን ከመሳሰሉ ሀገራት ይምጡ እንጂ ማለታቸውን ተከትሎ የአሜሪካ የምክር ቤት አባላትን ጨምሮ በመላው አለም ቁጣ መቀስቀሱ አይዘንጋም።

የአፍሪካ ህብረትም እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በጥር 12/2018 ባወጣው መግለጫው ዶናልድ ትራምፕ መላው የአፍሪካ ህዝብ እንዲሁም በመላው አለም የሚገኙ ትውልደ አፍሪካውያንን ይቅርታ እንዲጠይቁ ማሳሰቡ ይታወሳል።

ዶናልድ ትራምፕ ከአፍሪካ ተጨማሪ ስደተኛ በተለየ ሁኔታ እንዲመጣ የቀረበውን ሃሳብ በጠንካራ ቃላት ተቃወምኩ እንጂ አፍሪካውያንና ሃይቲያውያንን ውዳቂ ብዬ አልጠራሁም በማለት በቲውተር ገጻቸው አስተባብለዋል።

ሆኖም ሲ ኤን ኤንን የመሳሰሉ የአሜሪካ መገናኛ ብዙሃን በመረጃ ምንጮቹ ታማኝነት ላይ አጽንኦት ከመስጠት ባሻገር የትራምፕን የምርጫ ቅስቀሳና መሰል ማስረጃዎችን እያጣቀሱ ማስተባበያውን አጣጥለውታል።

ለትራምፕ አድናቆታቸውን የቸሩት ፕሬዝዳንት ዮዌሪ ሙሴቬኒ ግን ከአድናቆታቸው በላይ ለትችት የዳረጋቸው በሀገራቸው ለፕሬዝዳንትነት ለመወዳደር የዕድሜ ገደብ የሚያስቀምጠውን ህገ መንግስት ያሻሻሉብት ጉዳይ ነው።

ከትራምፕ አድናቆት በፊት መጀመሪያ የሀገራቸውን ችግር መፍታት ነበረባቸው የተባሉት ዮዌሪ ሙሴቬኒ  

ልጃቸውንና ባለቤታቸውን በተተኪነት ጭምር በማዘጋጀት በዩጋንዳ የአንድ ቤተሰብ መንግስት ለማቋቋም እየተንቀሳቀሱ ነው በሚል ሌላ ውዝግብ ውስጥ መግባታቸው ይታወቃል።