የፍኖተ ሰላም ባለስልጣናት ለተፈናቃዮች መጠለያ አዘጋጅተን ሰጥተናል አሉ

መጋቢት ፳፬ (ሀያ አራት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም 

ኢሳት ዜና:-ከቤንሻንጉል ጉሙዝ ተፈናቅለው በምእራብ ጎጃም ዞን በፍኖተ ሰላም ከተማ ሰፍረው የሚገኙት የአማራ ተወላጆች በቂ መጠለያ፣ በቂ ህክምናና በቂ ምግብ ማግኘታቸውን የዞኑ የምግብ ዋስትና እና የጸጥታ ዘርፍ ሀላፊዎች ገልጸዋል።

ው አቶ ያዛቸው በላይ ለኢሳት እንደገለጡት በከተማው የሚገኙት ተፈናቃዮች ለህክምና በሚመች ቦታ የኮብል ስቶን ድንጋይ ማምረቻ በነበረ ግቢው ውስጥ እንዲሰፍሩ ተደርጓል።

አቶ ያዛቸው እንዳሉት ተፈናቃዮች በሁለቱ ክልሎች መካከል የሚደረገው ውይይት ተሳክቶ ሰዎቹ ወደ መጡበት ቦታ እስከሚመለሱ ድረስ በቦታው ይቆያሉ። ይሁን እንጅ ተፈናቃዮች ወደ መጡበት ቦታ ስለመመለሳቸው በእርግጠኝነት ለመናገር እንደማይችሉና በሁለቱ ክልሎች መካከል የሚካሄደው ንግግር ውጤት እንደሚወስነው ገልጸዋል።

የፌደራል ፖሊስ አባላት በተፈናቃዮችን ዙሪያ ጥበቃ እያካሄዱ መሆናቸውን ለማወቅ ተችሎአል።  የከተማዋ የጸጥታ ዘርፍ ሀላፊ የሆኑት አቶ አሸብር ተፈናቃዮች ፍኖተሰላም ከተማ ከደረሱ በሁዋላ የጸጥታ ችግር አለመድረሱን ተናግረዋል።

በስፍራው የሚገኙ አርሶአደሮች  ያለመጠለያ ሜዳ ላይ እንዲወድቁ መደረጋቸውን በምሬት መናገራቸውን መግለጻችን ይታወሳል።