የፌድራል ፖሊሶች ህፃን በናትዋ ጀርባ ላይ እንዳለች በዱላ መተው መግደላቸው ተዘገበ

ህዳር ፯ (ሰባት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በሀና  ማሪያም  አካባቢ  መንግስት  የሚያደርገውን  መኖሪያ  ቤቶችን  የማፍረስ ዘመቻ  አስፈፃሚ  የሆኑ  የፌድራል  ፖሊሶች  ህፃን  በናትዋ  ጀርባ  ላይ  እንዳለች  በዱላ  መተው  መግደላቸው  ተዘገበ።

ከ30.000 ሺህ  በላይ   አባ ወራ  በተፈናቀለበት  የንፋስልክ  ላፍቶ  ክፍለ ከተማ ወረዳ 01  መኖሪያ  ቤቶችን  የማፍረስ  ዘመቻ   ትላንት  በናትዋ  ጀርባ  እንዳለች በፌድራል ፖሊስ  ተመታ  ከሞተችው   ህፃን  ጋር  የሞቱት  ቁጥር  አራት  ደርሰዋል።

መጠለያም  ሆነ  ተለዋጭ  ቤት  ሳያገኙ  ቤታቸውን  ከነንብረታቸው  በግሬደር እየተደረመሰ  ያለው  የወረዳ  01  ነዋሪዎች   ለብርድና  ለሀሩር  ከመዳረጋችን አልፎ  በፌድራል ፖሊሶች  የሚደርስባቸው  ድብደባ  ፣  እስራትና  ግድያ  ባስቸኮይ  እንዲቆምላቸው   ጥሪ  አድርገዋል ።

 

በፌድራል  ፖሊስ  ወደ  ተገደለችው  ህፃን  መጠለያ  ለቅሶ  ለመድረስ  እንኮን አልተፈቀደልንም  ያሉ  ነዋሪዎች  መንግስት  የበደል በደል  እየፈፀመብን  ነው ሲሉ  ምሬታቸውን  ገልፀዋል።

በንፋስልክ  ላፍቶ  ክፍለ  ከተማ  ወረዳ  01  ከሳምንት በላይ  በዘለቀው  ቤቶችን የማፍረስ  ዘመቻ  ከ30 ሺህ  በላይ  ቤቶች  ፈርሰው  ከ100 ሺህ  በላይ  ሰዎች  ከቤት  ንብረታቸው  ተፈናቅለው  በሜዳ  ላይ  ወድቀው  እንደሚገኙ  ካአካባቢው  ሰዎች  የሚደርሰን  መረጃ  ያመለክታል።

በዚህ  የማፍረስ  ዘመቻ  ቤተክርስቲያንና  መስኪድ  ሳይቀር መፍረሳቸውንም መዘገባችን  ይታወሳል።