የግብጽ መከላከያ የ48 ሰዓታት የጊዜ ገደብ ሰጠ

ሰኔ ፳፬ (ሃያ አራት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና :-የፕሬዚዳንት ሙሀመድ ሙርሲን አስተዳደር ያልተቀበሉት የተቃዋሚ ፓርቲ ደጋፊዎች ፣ ሞካታም እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የሚገኘውን የገዢውን ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት በመዝረፍ በርካታ ንብረቶችን ማውደማቸውን ተከትሎ፣ የአገሪቱ መከላከያ መንግስት እና ተቃዋሚዎች ችግራቸውን በ48 ሰአታት ውስጥ የማይፈቱ ከሆነ፣ የራሱን የሰላም የመፍትሄ ሀሳብ እንደሚያስቀምጥ አስታውቋል።

የአገሪቱ ጦር  ያወጣው መግለጫ የሙርሲ የአንድ አመት የስልጣን እድሜ ማክተሙን የሚያሳይ ነው በማለት አንዳንዶች ግምታቸውን እያሰፈሩ ነው።

በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ተቃዋሚዎች እሁድ እለት በተለያዩ ከተሞች ተቃውሞአቸውን ሲያሰሙ ውለዋል። ፕሬዚዳንት ሙርሲ እስከ ማክሰኞ 11 ሰአት ድረስ ስልጣን እንዲለቁ ተቃዋሚዎች የጠየቁ ሲሆን፣ ስልጣን ካልለቀቁ ግን ሰላማዊ እምቢተኝነት ሊከተል እንደሚችል አስጠንቅቀው ነበር።

ፕሬዚዳንት ሙርሲ ባለፈው አንድ አመት የፓርቲያቸውን አላማ ከማስፈጸም ውጭ ለአገሪቱ የሰሩት ስራ የለም በሚል ተቃዋሚዎች ይከሷቸዋል። ፕሬዚዳንቱ ከተቃዋሚዎች ጋር ለመነጋገር ያደረጉትን ግብዣም ተቃዋሚዎች ግማሽ መፍትሄ አንቀበልም በሚል ውድቅ አድርገዋል። ፕሬዚዳንቱ በበኩላቸው ተቃዋሚዎች ህገ-መንግስቱን ካልተቀበሉና ከህገ- መንግስቱ   ውጭ ከሄዱ እርምጃ እንደሚወሰዱ አስጠንቅቀዋል።