የግብጹ መሪ የአገሪቱን ዳኞች ሊያነገግሩ ነው

ህዳር ፲፯ (አስራ ሰባት) ቀን ፳፻፭  ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የግብጽ ፕሬዚዳንት ሙሀመድ ሙርሲ ባለፈው ሳምንት ያወጡትን አዲስ ድንጋጌ የተቃመው ግብጻውያን አደባባይ በመውጣት ተቃውሞአቸውን መግለጻቸውን ተከትሎ ነው ፕሬዘዳንቱ ከከፍተኛ ዳኞች ጋር ለመነጋገርና ችግሩን ለመፍታት ቃል የገቡት።

ፕሬዚዳንቱ ያወጡት ህግ ዳኞች እርሳቸው የሚያወጡትን ህግ እንዳይቀለብሱ የሚያስጠነቀቅ ነው። ይህን ድንጋጌ የተቃወሙ ዳኞች ህዝቡን ለተቃውሞ ጠርተዋል።

ያልተጠበቀ ተቃውሞ የገጠማቸው አዲሱ ፕሬዚዳንት ውሳኔው በዲሞክራሲአዊ መንገድ የተመረጡትን መሪዎች ለመከላከል፣ አብዮቱን ለመጠበቅ የተወሰደ ጊዜያዊ እርምጃ ነው ቢሉም ህዝቡ ግን የሚቀበለው አልሆነም።

ፕሬዚዳንቱ በፍጥነት ችግሩን ለመፍታት ካልቻሉ፣ አገሪቷ ተመልሳ ብጥብጥ ውስጥ ልትገባ እንደምትችል ነው የፖለቲካ ተንታኞች እያስጠነቀቁ የሚገኙት።