የጅንካ ነዋሪዎች የተቃውሞ ሰልፍ አደረጉ

መስከረም ፲፭(አሥራ አምስት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በደቡብ ኦሞ ዞን በጅንካ ከተማ በአይነቱ ልዩ ነው ተባለ የተቃውሞ ሰልፍ መደረጉን የአካባቢው ምንቾች ገልጸዋል።

የተቃውሞ ሰልፉ የተደረገው ከጅንካ ከተማ  ወደ ሃና በመጓዝ ላይ የነበረ አንድ ሰራተኛ መገደሉን ተከትሎ ነው። ሃና አዲሱ የስኳር ፋብሪካ ግንባታ የሚካሄድበት ቦታ ሲሆን፣ ግድያውን የፈጸሙትም የስኳር ልማቱ ከቀያቸው ያፈናቀላቸው

የሙርሲ ብሄረሰብ አባላት ሳይሆኑ እንደማይቀር ይገመታል። የጅንካ ተወላጁ ኡመር ንጋቱ  አይሱዚ መኪና ይዞ ለስራ ከሄደ በሁዋላ ሲመለስ በጥይት ተደብድቦ እንደተገደለ ታውቋል። ድርጊቱን ተከትሎ የከተማው ነዋሪዎች ” ቀጣዩ ሟች

ማን ይሆን፣ የጅንካ ህዝብ መብት የለውም ወይ? ለህይወታችን እንሰጋለን፣ ዝም አንልም” የሚሉ መፈክሮችን ይዘው ተቃውሞቸውን አሰምተዋል። የከተማው ነዋሪዎች ከዚህ ቀደም ተደጋጋሚ ግድያዎች ቢፈጸሙም በመንግስት በኩል

የተወሰደ እርምጃ አለመኖሩን የከተማው ነዋሪዎች ይናገራሉ።

በጉዳዩ ዙሪያ ያነጋገርናቸው የአንድነት ፓርቲ አካባቢው ተወካይ አቶ ስለሺ ጌታቸው መንግስት የአካባቢውን አርብቶአደሮች  ሳያማክር በማናለብኝነት የጀመረው የስኳር ፕሮጀክት ለዜጎች ህይወት መጥፋት ምክንያት እየሆነ መምጣቱን ይናገራሉ።

የአሜሪካ ኮንግረስ በዞኑ የሚካሄደው ስራ በአርብቶአደሮችን ህይወት  ላይ ችግር የሚፈጥር መሆኑ ከተረጋጋጠ ለኢትዮጵያ የሚሰጠው እርዳታ እንዲቋረጥ ወስኖ ነበር። የተለያዩ አለማቀፍ ድርጅቶችም የኢትዮጵያ የመከላከያ ሰራዊት አባላት በአርብቶ

አደሩ ህዝብ ላይ ጭካኔ የተሞላበት እርምጃ መውሰዳቸውን የሚያሳይ ሪፖርት ማውጣታቸው ይታወቃል።