የዳባት ወረዳ ነዋሪዎች ወልቃይትና ሴቲት ሁመራ እንደሚመለስላቸው ጠየቁ

የዳባት ወረዳ ነዋሪዎች ወልቃይትና ሴቲት ሁመራ እንደሚመለስላቸው ጠየቁ
(ኢሳት ዜና ሚያዝያ 09 ቀን 2010 ዓ/ም) ዳባት ከአመታት በፊት የነበራትን ሰባት ወረዳዎች በማጣት በሰሜን የነበሩትን አካባቢዎች ወደ ትግራይ ክልል እና ወደ ሰሜን ጎንደር ተከፋፍሎ በመሰጠቱ፤ ዛሬ ያላት የህዝብ ብዛት ተመናምኗል፡፡ ይህም ለልማት የሚመደብላትን ገንዘብ አነስተኛ እንዲሆን አድርጓል፡፡ እነዚህ ችግሮች ባለመነሳታቸው ከተማዋ ምንም ዓይነት ለውጥ ሳታመጣ ባለችበት መቆየቷ በየጊዜው በወረዳዋ ለሚከሰተው ችግር ምክንያት መሆኑን የዳባት ከተማ ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡
ሰሞኑን በዳባት ከተማ በተካሄደው ህዝባዊ ስብሰባ ከዳባት የተወሰዱ ወረዳዎች እዲመለሱና ልማቷ እንዲፋጠን ከወልቃይት ህዝብ ጋር በተለያዩ ጊዜያት ያቀረቡትን ጥያቄ እንዲመለስ ነዋሪዎች ጠይቀዋል፡፡ የገዥው መንግስት በየጊዜው ለሚነሱ የህዝብ ጥያቄዎች “ጀሮ ዳባ” በማለት ምላሽ አለመስጠቱ ህዝቡን ለቁጣ እንደጋበዘውና የተለያዩ እርምጃዎችን እንዲዎስድ ማድረጉን ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡
ለዳባት ነዋሪዎች ከፍተኛ የገቢ ምንጭ በመሆን ሲያገለግሉ የነበሩት ወልቃይትና ሰቲት ሁመራ ወረዳዎች ወደ ክልል አንድ መከለላቸው ነዋሪው የሚያገኘውን ጥቅም ያሳጣ በመሆኑ፣ በዘረፋ የተወሰዱት የወረዳዋ ከተሞች ሊመለሱ እንደሚገባ ህዝቡ በተለያዬ ስብሰባዎች ጥያቄውን ለገዥው መንግስት በተደጋጋሚ ማቅረባቸውን ገልጸዋል፡፡
የዳባት ህዝብ በስም እንደሚታወቀው “አስቸጋሪ!” የሚል ስም እንደተሰጠው የተናገሩት ቅሬታ አቅራቢ፣ በተደጋጋሚ የሚጠይቀው የወረዳዋ መሬቶች ይመለስልን ጥያቄ ምላሽ በመነፈጉ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የገዥው መንግስት ወልቃይትና ሁመራ አካባቢዎችን ወደ ትግራይ ክልል ሲከልላቸው፣ በወረዳዋ ነዋሪዎች ላይ ኢኮኖሚዊ ጉዳት ያደርሳል የሚል ግምት ባለማሰቡ ውሎ ሲያድር የወረዳዋ ወጣቶች ቁጣቸው ገንፍሎ ለመውጣቱ ምክንያት መሆኑን ቅሬታ አቅራቢው ለክልሉ አመራሮችና ለተሰበበው ህዝብ ገልጸዋል፡፡