የደህንነት ተቋማት ከፍተኛ በጀት ተመደበላቸው

ሰኔ ፫ (ሦስት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-መንግስት ለ2008 ዓም ከመደበው በጀት ውስጥ መከላከያ ሚኒስቴር፣ የፌዴራል ፖሊስ፣ ፍትህና ደህንነት ከፍተኛ ገንዘብ ተመድቦላቸዋል።
የፌዴራል መንግሥት የመደበኛ ወጪ ዝርዝር እንደሚሳየው የሀገር መከላከያ ሚኒስቴር 9. 5 ቢሊየን ብር፣ የፌዴራል ፖሊስ 1. 6 ቢሊየን ብር፣ ፍትሕና ደህንነት 3. 5 ቢሊየን ብር ከፍተኛ በጀት ተመድቦላቸዋል፡፡
መከላከያ በ2007 ዓም ከተያዘለት በጀት ጋር ሲነጻጸር የዘንድሮው በጀቱ በ 1 ቢሊየን 600 ሚሊዮን ብር ከፍ ብሎአል። ጦርነት የለም በሚባልበት ሁኔታ የመከላከያ በጀት ከአመት አመት መጨመሩ ሪፖርቱን አነጋገሪ ማድረጉን ዘጋቢያችን
ገልጿል። የ2008 በጀት ከ27 ቢሊዮን ብር በላይ የበጀት ጉድለት አሳይቷል። ኢህአዴግ መራሹ መንግስት የ2007 ምርጫ መቶ በመቶ በሕዝብ ተመርጦ ማሸነፉን በምርጫ ቦርድ በኩል ከታወጀ በሁዋላም
ሁከት ሊቀሰቅሱብኝ የችላሉ ያላቸውን የቀድሞ የአንድነት ፓርቲ፣ የመኢአድና የሰማያዊ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎችን እያሳደደ ማሰሩን አጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን፣ ለደህንነት ተቋማት የሚመደበው በጀት መጨመር ከዚሁ ጋር ሊያያዝ እንደሚችል
ዘጋቢያችን አስተያየቱን አስፍሯል።