የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች መንግስት ያዘጋጀውን የአዲስ አበባ ካርታ እየተቃወሙ ነው

ሚያዚያ ፳ (ሃያ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የአዲስ አበባ መስተዳደር የከተማዋን የመሬት ችግር ይቀርፋል በሚል ያዘጋጀውን አዲስ ካርታ በአምቦ፣ በጅማ፣ በነቀምት እና በተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች የሚማሩ ተማሪዎች እየተቃወሙት ነው።
በወለጋ የፌደራል ፖሊስ አባላት በወሰዱት እርምጃ በተማሪዎች ላይ ጉዳት ደርሷል።
ተቃውሞውን በተመለከተ ጥያቄ ያቀረብንላቸው የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ምክትል ሊቀመንበርና የቀድሞ የፓርላማ አባል አቶ ገብሩ ገብረማርያም አቅጣጫ የያዘ ይሁን አይሁን ባይታወቅም ተቃውሞዎች እየታዩ መሆኑን ገልጸዋል።
አቶ ገብሩ የህዝብን ጥያቄ አንስቶ ተገቢውን መልስ መስጠት እንጅ የሚጣረሱ ነገሮችን ብቻ እያነሱ የእኛ መንገድ ብቻ ነው ትክክል ማለቱ እንደማያዋጣ ተናግረዋል። አቶ ገብሩ ችግሩ ወደ ብሄር ግጭቶች እንዳያመራም ጥንቃቄ እንዲደረግ አሳስበዋል።