የውጭ ጉዳይ ሚ/ር “የሚመለከታቸው አካላት ካልፈቀዱ በስተቀር አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ለመጎብኘት እንደማይቻል” ገለጸ

የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ለእንግሊዝ የአፍሪካ ክፍል ሃላፊ በጻፈው ደብዳቤ፣ አቶ አንዳርጋቸው የህግና የማማከር አገልግሎት እንዲያገኙ ለማድረግ ” የሚመለከታቸው አካላት” መፍቀድ አለባቸው ብሎአል። የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤቱ ” የሚመለከታቸው አካላት” ያላቸውን አካላት በስም ከመጥቀስ ተቆጥቧል። ይሁን እንጅ የመረጃው ምንጮች እንደሚሉት ” የሚመለከታቸው አካላት” የተባሉት የደህንነት ሰዎች ናቸው።

የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤቱ ይህን መልስ የጻፈው፣ የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት የአፍሪካ ክፍል ሃላፊ ” አቶ አንዳርጋቸውን የመጎብኘት” ፈቃድ እንዲሰጣቸው የጻፉትን ደብዳቤ ተከትሎ ነው።

የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት በመልሱ ማዘኑንና ተጨማሪ መልስ እየጠበቀ መሆኑን ለማወቅ ተችሎአል።

የኢህአዴግ የደህንነት አባላት አቶ አንዳርጋቸው እንዳይጎበኙና የምክር አገልግሎት እንዳይሰጣቸው የሚከለክሉት ፣ የአቶ አንዳርጋቸውን ስቃይ በማብዛት እና በስቃይ ውስጥ ሆነው የሚናገሩትን ለህዝቡ በማቅረብ

የህዝቡን የትግል ወኔ ለመስበር መሆኑን አንድ የቤተሰባቸው አባል ገልጸው፣ ይህንንም የእንግሊዝ  የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት እንዲያውቀው ማድረጋቸውን ተናግረዋል።

ለኢሳት የሚደርሱት መረጃዎች እንደሚያሳዩት አቶ አንዳርጋቸውን በእንቅልፍ እጦት በመቅጣትና የተለያዩ የስነ ልቦና ጫናዎች እንዲደርሱባቸው በማድረግ የማይፈለጉትን ነገር እንዲናገሩ ግፊት እያደረጉባቸው ነው።

እስካሁን ድረስ የሚደርስባቸውን ከፍተኛ ስቃይ ተቋቁመው ምንም አይነት መረጃ ባለመስጠታቸው የተበሳጩት የጸረ ሽብር ግብረሃይል የሚባለው ቡድን መሪዎች በአቶ አንዳርጋቸው ላይ ተጨማሪ የማሰቃያ

ዘዴዎች እንዲፈጸሙ ባለፈው ቅዳሜ በጠ/ሚንስትር ግቢ በተካሄደው ስብሰባ ውሳኔ አሳልፈዋል።

የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤትም ሆነ የአቶ ሃይለማርያም ጽህፈት ቤት ለቀረበለት የጉብኝት ጥያቄ መልስ አለመስጠቱ፣ የአቶ አንዳርጋቸው ጉዳይ ከጀርባ ሆነው አገሪቱን በሚገዙት ጥቂት ሰዎች እጅ መውደቁን ያሳያል

በማለት ጉዳዩን በቅርብ የሚከታተሉ ሰው ተናግረዋል።

በተመሳሳይ ዜና ደግሞ ህዝቡ አሁንም በአቶ አንዳርጋቸው መታሰር የተሰማውን ቁጭት እየገለጸ ነው። በጃፓን የሚገኙ ኢትዮጵያውያን እንዲሁ የተቃውሞ ሰልፍ አድርገዋል