የዋጋ ግሽበት እየጨመረ መሄዱን የመንግስት መረጃ አመለከተ

ሰኔ ፬ (አራት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ማእከላዊ ስታትስቲክስ ጽ/ቤት በወጣው መረጃ በዚህ አመት የታየው አጠቃላይ የዋጋ ግሽበት ካለፈው አመት ጋር ሲነጻጸር በ7 በመቶ ጭማሪ ሲያሳያስ ፣ የምግብ ያዋጋ ግሽበት 6.9 በመቶ
ምግብ ነክ ያልሆኑ ደግሞ 8 .2 በመቶ የዋጋ ጭማሪ አሳይተዋል።
በዚህ አመት በግንቦት ወር የታየው የዋጋ ግሽበት አምና ከነበረው ጋር ሲነጻጸር በ9.4 ከፍ ብሎአል። የግንቦት ወር 2007 ዓም የምግብ ዋጋ ግሽበት ከአምናው ተመሳሳይ ወር ጋር ሲነጻጸር በ10.1 በመቶ ጭመሪ ሲያሳይ፣ ምግብ ነክ
ያልሆኑ ደግሞ 8.7 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል።
በሁሉም የምግብ ክፍሎች ጭማሪ የታየ ሲሆን በተለይ ስጋ ፣ ወተት አይብና እንቁላል፣ ዜይትና ቅባቶች፣ አትክልት እና ጥራጥሬ፣ ፍራፍሬና ቅመማ ቅመም በተለይም ያልተፈጨ በርበሬ ላይ ጭማሪው ጎልቶ ታይቷል።
የበቆሎ፣ የማሽላና ስንዴ ዋጋ ላይ መጠነኛ ቅናሽ በመታየቱ የዳቦና እህል የዋጋ ግሽበት በ0.9 ከመቶ ቅናሽ ማሳየቱን ማእከሉ ገልጿል።
በጫት፣ በልብስና መጫሚያዎች፣ በኮንስትራክሽን እቃዎች በተለይም በስሚንቶ፣ የማገዶ እንጨት፣ የቤት እቃዎችና ቤት መስጌጫዎች ላይ የዋጋ ጭማሪ ታይቷል።
የችርችራኦ ዋጋ ጭማሪው በአዲስ አበባ 9.1 ከመቶ፣ በአፋር 12.7 በመቶ፣ በአማራ 5.6 በመቶ፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝ 2.3 በመቶ፣ ድሬዳዋ 17.8 በመቶ፣ ጋምቤላ 2.9 በመቶ፣ ሀረሪ፣ 10.8 በመቶ ኦሮምያ 16.1 በመቶ፣
ደቡብ 3.8 በመቶ ፣ ሶማሌ 13.9 በመቶና ትግራይ 6.1 በመቶ መሆኑን መስሪያ ቤቱ ገልጿል።
በሁሉም ክልሎች የምግብ ዋጋ ከ3 እስከ 18 በመቶ ጭማሪ ሲታይ በትግራይ ብቻ በ0.8 ቅናሽ አሳይቷል። የምግብ ዋጋ ጭማሪ በከፍተኛ ደረጃ የሚታየው በኦሮምያ ነው።
አብዛኛው የመንግስት ሰራተኛና ደሃው የህብረተሰብ ክፍል የሚያገኘው ገቢ ባለበት መቀጠሉ፣ በየጊዜው የሚጨምረውን የዋጋ ግሽበት ለመቋቋም አላስቻለውም።
መንግስት በስኳርና ዘይት ምርቶች ላይ ድጎማ በማድረግ እያከፋፈለ መሆኑ ይታወቃል።