የኦሮሞ ነጸናት ግንባር በቶሮንቶ የተሳካ ስብሰባ አደረገ

ሐምሌ ፫ (ሦስት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በብርጋዲየር ጄ/ል ከማል ገልቹ የሚመራው የአሮሞ ነጸናት ግንባር ባለፈው ቅዳሜ እንደ ፈረንጆቹ አቆጣጠር ጁላይ 6 ቀን 2012 በቶሮንቶ ካናዳ የተሳካ ህዝባዊ ስብሰባ አድረገ።

በዚህ በቶሮንቶ አካባቢ የሚገኙ የኦሮሞ ተወላጆችና ሌሎች ኢትዮጵያዊያን በተገኙበት የግማሽ ቀን ስብሰባ ላይ፤ የድርጅቱ የበላይ አመራር አካላት፡ ማለትም ብርጋዲየር ጄነራል ሀይሉ ጎንፋ ከአስመራ በስልክ፡ ዶ/ር ኑሮ ደደፎና የድርጅቱ ቃል አቀባይ የቀድሞ የኢትዮጵያ አየር ሀይል ባለሟል አቶ ተማም ባቲ፤ በአካል ተገኝተው፤ ንግግር በማድረግ ከተሰብሳቢው ጋር ተወያይተዋል።

ጄ/ል ሀይሉ ጎንፋ፤ መጀመሪያ በኦሮምኛ አጭር ንግግር ያደረጉ ሲሆን፤ ቀጥለውም በአማርኛ ኢትዮጵያ ውስጥ ስለሰፈነው ሁለገብ በደል አብራርተው፡ ሕወሀትን አስወግደን ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ ለመመስረት፤ የጋራ አላማ ይዘን መታገል አለብን ሲሉ ተናግረዋል። በስብሰባው ላይ፤ ጄኔራል ሀይሉ ከሰተብሳቢው ህዝብ ለተነሱት በርካታ ጥያቄዎች ምላሾችን ሰጥዋል።

ከጥያቄዎቹም መካከል፡ “ስማችሁን ለምን ከኦሮሞ ነጻነት ወደ ኢትዮጵያዊ ስም አልቀየራችሁም?” “ዛሬ ለኢትዮጵያ እንታገላለን ብላችሁ፤ ምናልባት ነገ ከነገወዲያ እንደ ኢህአዴግ ኢትዮጵያ ከገባችሁና ስልጣን ከያዛችሁ በሁዋላ የመገንጠሉን ጥያቄ ልትመለሱበት ነው ወይ?” የሚሉት ሲገኙበት፤ ጄኔራል ሀይሉ ጎንፋም “ኦነግ የተወለደበት ጭቆናዊ ምክንያትና ሁኔታ ሙሉ በሙሉ ስላልተቀየረ ስሙን እንያዘው እንጂ፤ ወደፊት ሁላችንም በእኩልነት የምንኖርባት ኢትዮጵያን ከመሰረትን ስሙ እንደሚቀየር፤ ኢትዮጵያ ኦሮሞ፡ ኦሮሞም ኢትዮጵያ እንደሆነ፡ ኦሮሞ ለኢትዮጵያ አንድነት በሞትና በመሰዋት የታወቀ እንደሆነና ማነም በጸረ-ኢትዮጵያነት ሊከሰው እንደማይችል፡ እንደውም ትናንት ከትናንት ወዲያ ደርግን ጨምሮ ለኢትዮጵያ አንድነት እንሞታለን የሚሉ አገር እንደከፋፈሉ፤ እኛ ግን አሁን መተማመንና አብረን መታገል እንጂ፤ እርስ በርስ መጠራጠር የለብንም” ብለዋል።

የጥምረቱ ም/ሊ/መ አቶ አሎ አይደሂስ ጥምረቱን ወክለው ባደረጉት ንግግር፡ ሐወሀት/ኢህአዴግ እንኩዋንስ የኢትዮጵያን ብሄር ብሄረሰቦች መብት ሊያስከብር፤ የራሱን የትግራይን ህዝብም በባርነት የሚያስተዳድር ስለሆን መወገድ አለበት ብለዋል።

በዚህ በአማርኛና በኦሮምኛ በተካሄደው ስብሰባ ላይ የመድረኩ መሪ አቶ ታደለ በኦሮምኛና በአማርኛ መድረኩን በተሳካ ሁኔታ ያስተናበሩ ሲሆን፤ እንደ አቶ ግርማ ቸሩና ሼክ መሀመድ ያሉ ሰዎች ምክርና መልእክቶችን አስተላልፈዋል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide