የኢጋድ አባል ሀገራት የደቡብ ሱዳንን ችግር ከመፍታት ይልቅ ብሔራዊ ጥቅማቸውን እያስቀደሙ ነው ተባለ

(ኢሳት ዜና–መስከረም 11/2010) የደቡብ ሱዳን አማጽያን መሪና የቀድሞው ምክትል ፕሬዝዳንት የኢጋድ አባል ሀገራት የደቡብ ሱዳንን ችግር ከመፍታት ይልቅ ብሔራዊ ጥቅማቸውን እያስቀደሙ ችግር መፍጠራቸውን ገለጹ።

ሬክ ማቻር በኢጋድ አባል ሀገራት ላይ ተስፋ መቁረጣቸውን ያስታወቁት ባለፈው ሀሙስ ለተባበሩት መንግስታት ዋና ጸሃፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ በጻፉት ደብዳቤ መሆኑን መረዳት ተችሏል።

የአማጽያኑ መሪ ዶክተር ሬክ ማቻር እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር መስከረም 14/2017 የጻፉትና በሱዳን ትሪቡን በኩል ይፋ የሆነው ደብዳቤ እንዳመለከተው የኢጋድ አባል ሀገራት የደቡብ ሱዳን ፕሬዝዳንት ሳልቫኬር የፈለጊትን እየፈጸሙ መሆናቸውን ያስረዳል።

የኢጋድ የሚኒስትሮች ምክር ቤት እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ሀምሌ 24/2017 ያዋቀረው መድረክ ተቃዋሚዎችን ያገለልና ሳልቫኬር እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በሀምሌ 9/2010 ይፋ ያደረጉትን እቅድ የሚደግፍ ነው ሲሉ ሬክ ማቻር የኢጋድን ገለልተኛ አለመሆን በጽሁፋቸው ላይ አስፍረዋል።

በመሆኑም ኢጋድ የሽምግልናው አካል መሆን ቢችል እንኳን ዋና ሸምጋይ ለመሆን ግን የሞራል ብቃት የለውም ብለዋል።

ኢጋድ ኢትዮጵያን ጨምሮ የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት የተሰባሰቡበት ቡድን መሆኑ ይታወቃል።