ሀገራት ከአምባገነኑ የህወሃት አገዛዝ ጋር ያላቸውን ግንኙነት እንዲመረምሩ ኢትዮጵያን ጠየቁ

(ኢሳት ዜና–መስከረም 11/2010)ካናዳ ከአምባገነኑ የህወሃት አገዛዝ ጋር ያላትን ግንኙነት እንድትመረምር በካናዳ የሚኖሩ ኢትዮጵያን ጠየቁ።

በጀርመን የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ደግሞ አሜሪካ ለህወሀት መንግስት የምታደርገውን ድጋፍ እንድታቆም ጠይቀዋል።

ኢትዮጵያውያኑ ጥያቄውን ያቀረቡት በካናዳ ቶሮንቶና በጀርመን ፍራንክፈርት ባካሄዱት የተቃውሞ ትዕይንት ነው።

እነዚህ የተቃውሞ ትዕይንቶች በዓለም ዓቀፍ ደረጃ በኢትዮጵያውያን ግብረ ሃይል የተዘጋጁ ሲሆን ባለፈው ሰኞ በዋሽንግተን ዲሲም መካሄዱ የሚታወስ ነው።

በዓለም ዓቀፍ የነጻነት ትግል ድጋፍ ጥሪ ግብረሃይል የተጠራው ሰላማዊ ሰልፍ በተለያዩ የአውሮፓና የሰሜን አሜሪካ ከተሞች ተካሂዷል።

ባለፈው ሰኞ በካናዳ ቶሮንቶ በተካሄደው ትዕይንተ ህዝብ ኢትዮጵያውያን በህወሀት መንግስት የሚፈጸሙትን የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን በማውገዝ የካናዳ መንግስት የሚያደርገውን ድጋፍ እንዲያቋርጥ ጠይቀዋል።

የኢሬቻውን ጭፍጨፋ አንደኛ ዓመት በማስታወስ በተካሄደው በዚሁ ትዕይንተ ህዝብ በህወሀት መንግስት በየማጎሪያ እስርቤቶች የሚሰቃዩትን ጋዜጠኞች፣ የፖለቲካ መሪዎችንና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾችን ስም በማንሳት የካናዳ መንግስት በህወሀት ላይ ጫና እንዲፈጥር ጥሪ አድርገዋል።

የምዕራቡ ዓለም የመገናኛ ብዙሃና በኢትዮጵያ እየተካሄደ ስላለው መጠነ ሰፊ የሰብዓዊ መብት ጥሰትና የጅምላ ግድያ ትኩረት እንዲሰጡትም ኢትዮጵያውያኑ መጠየቃቸው ታውቋል።

ዛሬ በጀርመን ፍራንክፈርት ተመሳሳይ ዓላማ ያነገበ ትዕይንተ ህዝብ በኢትዮጵያውያን የተካሄደ ሲሆን ለአሜሪካና ለጀርመን መንግስታት መልዕክት እንደተላለፈላቸው አዘጋጅ ኮሚቴው ለኢሳት አስታውቋል።

ኢትዮጵያውያኑ የኢሬቻን ጭፍጨፋ በማስታወስ ተጠያቂ የሚሆኑ የህወሀት መንግስት ባለስልጣናት ለፍርድ እንዲቀርቡ፣ በኢትዮጵያ የሚካሄደው የዘር ግጭት ወደ ከፋ ደረጃ ከመድረሱ በፊት ምዕራባውያን መንግስታት አስቸኳይ እርምጃ እንዲወስዱ ጠይቀዋል።

በአሜሪካን ኮንግረስ ፊት የሚቀርበውን ኢትዮጵያን በተመለከተ ለተዘጋጀው ሰነድ ድጋፋቸውን ሰጥተዋል።

ፍራንክፈርት በሚገኘው የአሜሪካን ኤምባሲ ደጃፍ በጀመረው ተቃውሞ ኢትዮጵያውያን የአሜሪካን መንግስት ከህወሀት አንጻር የሚከተለውን ፖሊሲ አጥብቀው አውግዘዋል።

አሜሪካ በኢትዮጵያ የሚፈጸመውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት በገንዘብ መደገፍ አቁሚ፣ ከኢንቨስትመንት በፊት የህግ የበላይነት እንዲሰፍን ጫና ፍጥሪ፣ ሁሉም የህሊና እስረኞች ነጻ እንዲሆኑ በአገዛዙ ላይ አቋም ውሰጂ የሚሉና ሌሎች መልዕክቶች የተላለፉ ሲሆን ወደ ፍራንክፈርት ከተማ ከንቲባ ጽ/ቤት በማምራትም ለጀርመን መንግስት ተመሳሳይ መልዕክት ማስተላለፋቸውን ለማወቅ ተችሏል።