የኢትዮጵያ መንግስት በየወሩ 45ሺህ የቤት ሠራተኞችን ወደ ሳዑዲ እንደሚልክ ተገለፀ

 

ሚያዚያ ፭ (አምስት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በሳዑዲ አረቢያ/ ጄዳ  የኢትዮጵያ ኤምባሲ  የሚገኝ የዉስጥ አዋቂ ምንጭን በመጥቀስ በቀረበዉ በዚሁ መረጃ መሰረት ኢትዮጵያ ሠራተኞቹን ለመላክ የሚያስችሏትን መሰናዶዎች በማድረግ ላይ እንደምትገኝ ተገልጿል።

አሻ-አርክ አል አዉሳት ጋዜጣ እንደገለፀዉ የሳዑዲ አረቢያ መንግስት ኬንያን ጨምሮ ከአራት መንግስታት ጋር የቤት ሰራተኞችን ለመመልመል የጀመረዉ ስምምነት አጥጋቢ ባለመሆኑ ዉለታዉን ካቋረጠ በሁዋላ ኢትዮጵያዉያን የቤት ሰራተኞችን ለመቅጠር ያለዉ ፍላጎት በከፍተኛ ደረጃ ጨምሯል።  

የሳዑዲ የኢኮኖሚክ ጉዳዮች የጄዳ ምክትል ካዉንስለር መ/ቤታቸዉና የኢትዮጵያ የሠራተኛ ሚኒስቴር የኮሚቴ አባላት የቤት ሰራተኞቹ በኢትዮጵያ በቂ ስልጠና ከወሰዱ በሁዋላ ወደ ሳዑዲ አረቢያ የሚጓጓዙበትን ሁኔታ ለማመቻቸት በርካታ ግንኙነቶች ማድረጋቸዉን ገልፀዋል።  የሳዑዲ ቤተሰቦች ኢትዮጵያዉያን ሰራተኞችን ለመቅጠር ያላቸዉን እየጨመረ የመጣ ፍላጎት በመረዳት 1200 ለሚሆኑ ተጓዦች አስፈላጊዉ የተጠናቀቀ ሲሆን በሳዑዲ ልማድና ባህል መሰረት ኢትዮጵያዉያኑ ተገቢ ስልጠና መዉሰዳቸዉ ከስራቸዉ የሚጠፉ ያላቸዉን አሃዝ ዝቅ እንደሚያደርገዉ አስረድተዋል። 

ኢትዮጵያዉያን የቤት ሰራተኞች የበለጠ ክፍያ ከግል ኩባንያዎችና ደላሎች ለማግኘት ከስራ ገበታቸዉ እንዳያመልጡ ጥናትና ዉይይት የተደረገበት ሲሆን ይህን በሚያደርጉት ላይ ቅጣት እንደሚኖር የገለፁት ምክትል ካዉንስለር ሰራተኞቹ ከቤተሰባቸዉና ከኤምባሲዉ ጋር እንዲገናኙ ተንቀሳቃሽ ስልክ እንዲጠቀሙ የሚያስችል ስምምነት በስራ ኮንትራታቸዉ ላይ እንዲቀመጥ የኢትዮጵያ የሰራተኛ ሚኒስቴር እንደሚፈልግ አልሸሸጉም።  

ይህ በእንዲህ እንዳለ በኩዌት አንዲት ኢትዮጵያዊ የቤት ሰራተኛ ጃህራ በተባለዉ በረሃማ አካባቢ እንደተጠለፈችና የአስገድዶ መድፈር ወንጀል እንደተፈፀመባት እንዲሁም  የያዘችዉ ገንዘብ የተዘረፈባት መሆኑን አረብ ታይምስ የመረጃ ምንጭ ገልጿል።  የኩዌት የአገር ዉስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር በደረሰዉ መረጃ መሰረት ወንጀሉን የፈፀመዉን ግለሰብ ለመያዝ ጥረት በማድረግ ላይ መሆኑ ታዉቋል።  

ይኸዉ የመረጃ ምንጭ በሌላ በኩል  በኩዌት ሳባህ አል ሳልም ነዋሪ የሆነች አንዲት ሴት ዕድሜያቸዉ ስድስትና ሰባት የሆነ ሁለት የልጅ ልጆቻቸዉ የኤች አይ ቪ ኤድስ በሽተኞች እንደሆኑ በመግለፅ ህፃናቱ የበሽታዉ ተጠቂ የሆኑት ከሁለት አመት በፊት ቀጥረዉ ያሰሯት ከነበረችዉ ኢትዮጵያዊት የተላለፈ ሊሆን እንደሚችል መግለፃቸዉን አስታዉቋል። 

ይህን የደረሱበት አንድ የሳዑዲ ሰዉ ወደ አገሯ ሊመልሳት በመዘጋጀት ላይ መሆኑን በመረዳት ከቤቱ የጠፋቸዉ ኢትዮጵያዊ የቤት ሰራተኛ የኤች አይ ቪ ኤድስ በሽተኛ እንደሆነችና ሰዎች እንዳይቀጥሯት በማስጠንቀቅ  ከነፎቶግራፏ በኢንተርኔት ያሰራጨዉን መረጃ በማየታቸዉ መሆኑ ተገልጿል።

ኢትዮጵያዉያን የቤት ሰራተኞች በአረብ አገራት የሚደርስባቸዉን ግፍና መከራ በተመለከተ ነዋሪነታቸዉ በኖርዌይ ድራመን ከተማ የሆነ ወ/ሮ አይሪን ካርል-ሰን “ እንዴት ኢትዮጵያዉያን ሴቶችና ልጃገረዶች በራሳቸዉ መንግሰት ለባርነት ይሸጣሉ? ይህ የመለስ ዜናዊ መንግሰት አዲስ ዘግናኝ ድርጊት ነዉ።” በማለት ገልፀዉታል።

___________________________________________________________________________________________________ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide