የኢትዮጵያ መንግስት በውጭና በአገር ውስጥ የሚገኙ ፖለቲከኞችንና ጋዜጠኞችን ይሰልላል ተባለ

መጋቢት ፲፮ (አስራ ስድስት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ሂውማን ራይትስ ወች ባወጣው ጋዜጣዊ መግለጫ የኢትዮጵያ መንግስት የውጭ ቴክኖሎጂን በመጠቀም በአገር ውስጥ እና በውጭ የሚኖሩ ፖለቲከኞችንና ጋዜጠኞችን ይሰልላል ብሎአል።

ድርጅቱ ባወጣው ባለ 100 ገጽ ሪፖርት፣ የኢትዮጵያ መንግስት ለስርአቱ አደገኛ ናቸው ብሎ የሚያስባቸውን  በውጭና በአገር ውስጥ ያሉ ተቃዋሚዎችን ለመሰለል ከተለያዩ አገሮች ቴክኖሎጂዎችን ማስገባቱን ” ገልጿል።

የመንግስት ድርጊት ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ፣ በነጻነት የመደረጃትና መረጃ የማግኘት መብት እንደሚጥስ የገለጸው ሂውማን ራይትስ ወች፣ መንግስት ሙሉ በሙሉ በሚቆጣጠረው ቴሌኮሚኒኬሽን አማካኝነት የስለላ ስራው እንደሚሰራ አመልክቷል።

ለኢትዮጵያ መንግስት የቴክኖሎጂ ውጤቶችን የሚሸጡ ድርጅቶች ፣ መንግስት በህገ ወጥ መንገድ ለሚያደርገው ስለላ ድጋፍ እየሰጡ ነው” በማለት የድርጅቱ የቢዝነስና የሰብአዊ መብቶች ዳይሬክተር የሆኑት አርቪድ ጋንሲያን ተናግረዋል።

ሪፖርቱ ጉዳት የደረሰባቸውን ሰዎች እንዲሁም የቀድሞ የደህንነት ሰራተኞችን በማነጋገር የተጠናቀረ ነው፤፡መንግስት በወንጀል የጠረጠራቸውን ሰዎች አስሮ በሚያሰቃይበት ጊዜ ያለፍርድ ቤት ትእዛዝ የጠለፋቸውን ስልኮች በማስረጃነት አቅርቦ እንደሚያሰማ እንዲሁም ሰላማዊ  የተቃውሞ ሰልፎች በሚደረጉበት ጊዜ የስልክ መስመር ( ኔት ወርክ) እንደሚጠፋ ድርጀቱ በሪፖርቱ አመልክቷል።

ለስለላ ተግባር የሚውሉት አብዛኞቹ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ከቻይናው ዜቲኢ መገኘቱን  ሪፖርት፣አመልክቷል፡፡ እንዲሁም ተቀማጭነቱን በዩናይትድ ኪንግደምና በጀርመን ካደረገው ጋማ ኢንተርናሽናል ፊን ፊሸርን፣ ከጣሊያኑ ሃኪንግ ቲም ከርቀት ለመቆጣጠር የሚያስችል መሳሪያ አግኝታለች።