የአዲስ አበባ ፖሊሶች የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችንና ደጋፊዎችን ለማስፈራራት ሙከራ እያደረጉ ነው

ሚያዚያ ፲፯ (አስራ ሰባት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በመጪው እሁድ በጃንሜዳ ለሚካሄደው የተቃውሞ ሰልፍ የአዲስ አበባ መስተዳድር እውቅና ቢሰጥም ፣ የአዲስ አበባ መስተዳድር ፖሊሶች ህዝቡ በብዛት እንዳይገኝ ለማድረግ የማስፈራሪያ እርምጃ እየወሰዱ መሆኑን የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ ወጣት ብርሃኑ ተክለ ያሬድ ገልጿል።

ወጣት ብርሃኑ እንዳለው የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽነር በሰልፉ ላይ አንድም ነገር ቢከሰት እንዲሁም ከተሰጣችሁ ጊዜ አንድ ማይክሮ ሰከንድ ብታልፉ ሰልፉን እንበትናለን በማለት ለማስፈራራት ሞክረዋል።

ማስፈራሪያውን የሰጡት የፖሊስ አዛዡ በስም ይታወቁ እንዲሆን ጥያቄ የቀረበለት ወጣት ብርሃኑ፣ ኮሚሽነሩ ማንነቱን የሚገልጽ መረጃ በጠረጴዛው ላይ ባለማስቀመጡ ስሙን ለማወቅ እንዳልተቻለ፣ ነገር ግን ቢሮው ውስጥ አብረው የነበሩትን ኮሚሽነር እንደሚያውቃቸው ገልጿል

ቅስቀሳው በጥሩ ሁኔታ እየተካሄደ ና የህዝቡም ማበረታቻ ጥሩ መሆኑን  የገለጸው ወጣት ብርሃኑ ፣ ነገር ግን  በቅስቀሳ ላይ የነበሩ 25 አባሎቻቸው ታስረው እስካሁን አለመፈታታቸውን ገልጿል።

ወጣት ብርሃኑ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ ግብ ሳይሆን ወደ ቀጣዩ ትግል መሸጋገሪያ መሆኑን ገልጾ ፣ የአዲስ አበባ ህዝብ በነቂስ ወጥቶ ድምጹን ያሰማል ብሎ እንደሚያምን ተናግሯል።

ስቱዲዮ ከመግባታችን በፊት በደረሰን ዜና ደግሞ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች የሆኑት ሊቀመንበሩ ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት፣ ምክትሉ አቶ ስለሺ ፈይሳ እና የህዝብ ግንኙነት ሃላፊው አቶ ብርሃኑ ተክለ ያሬድ በፖሊስ ተይዘው ወደ እስር ቤት ተጉዘዋል። ወደ እስር ቤት እየተጓዙ በነበረበት ወቅት ኢንጂነር ይልቃልን አነጋግረነው ነበር።