የአሜሪካ የኮንግረስ አባላት ያጸደቁት ኤች አር 128 በመባል የሚጠራው ህግ ሉአላዊነትን የሚጥስ ነው በማለት አገዛዙ ተቃውሞውን ገለጸ

የአሜሪካ የኮንግረስ አባላት ያጸደቁት ኤች አር 128 በመባል የሚጠራው ህግ ሉአላዊነትን የሚጥስ ነው በማለት አገዛዙ ተቃውሞውን ገለጸ
(ኢሳት ዜና ሚያዝያ 03 ቀን 2010 ዓ/ም) የአሜሪካ የኮንግረስ አባላት በኢትዮጵያ ስብአዊ መብት እንዲከበር ለማስገደድ ያጸደው ህግ በርካታ ለነጻነታቸው የሚታገሉ ዜጎችን ያስደሰተ ቢሆንም፣ በአገዛዙ በኩል ግን በበጎ መልኩ አልታዬም።
ይህ በርካታ አስገዳጅ አንቀጾችን የያዘው ህግ በኦሮምያና በአማራ ክልሎች የተፈጸሙት ግድያዎችና አፈናዎች በተመድ ገልለተኛ አጣሪዎች እንዲጣራ፣ እስረኞች በሙሉ እንዲፈቱ እንዲሁም ሁሉንም አሳታፊ የሆነ የፖለቲካ ስርዓት እንዲፈጠር ይጠይቃል።
ህጉ የአገሪቱን ሉአላዊነት የሚዳፈር ነው በማለት አገዛዙ ተቃውሞውን ገልጿል።አገዛዙ ህጉ እንዳይጸድቅ ከፍተኛ በጀት መድቦ በአንዳንድ የኮንግረስ አባላት አማካኝነት ግፊት ሲያደርግ ቢቆይም ህጉን ከመጽደቅ ሊያስቀረው አልቻለም። የውሳኔ ሃሳቡ “የአሜሪካ እና የኢትዮጵያን የሁለትዮሽ ግንኙነትና የጋራ ጥቅም ከግምት ውስጥ ያላስገባ እና አፍራሽ” ነው ሲል የጠቀሰው አገዛዙ፣ በተለይ ለአዲሱ ጠ/ሚኒስትር የለውጥ እንቅስቃሴ እድል ያልሰጠ ነው ብሎአል።
ህጉ መጽደቁን ተከትሎ ህጉ እንዲጸድቅ ከፍተኛ ስራ ሲሰሩ የነበሩ በአሜሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ደስታቸውን ገልጸዋል።
የኮሎራዶ ኮንግረስማን ሚክ ኮፍማንና የኒውጀርስ ምክር ቤት አባል ክሪስ ስሚዝ ለህጉ መጽደቅ ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል።
በኢትዮጵያ የሚፈጸመውን የሰብአዊ መብት ጥሰት በማጋለጥ ከሚታወቁት አንዱ የሆነው የኦክላንድ ኢንስቲቱይት እርምጃውን አድንቋል።ይህ በ108 የኮንግረስ አባላት የተደገፈው ውሳኔ በኢትዮጵያ የሰብአዊ መብቶች እንዲከበሩና ሁሉን አሳታፊ የሆነ መንግስት እንዲፈጠር የሚጠይቅ ነው ብሎአል።
አሜሪካ ለረጅም አመታት በኢትዮጵያ ሲፈጸም የነበረውን የሰብአዊ መብት ጥሰት እንዳላዬች ሆና መቆየቷን የጠቀሰው ኦክላንድ ኢንስቲትዩት፣ ኮንግረሱ ያለፉ ስህተቶችን ለማስተካከል የወሰደውን እርምጃ አድንቋል።
ታዋቂው የሰብአዊ መብት ድርጅት ሂውማን ራይትስ ወች ባወጣው መግለጫ ደግሞ ውሳኔው በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ጫና የሚያሳድር መሆኑን ጠቅሷል። ይህ አሳሪ ያልሆነ ህግ፣ በቅርቡ በኢትዮጵያ የሚገኘው የአሜሪካ ኢምባሲ ካወጣው ህግ ጋር ተደማምሮ ፣ አሜሪካ ጠንካራ የሆነ የፖለቲካ ማሻሻያ እንዲደረግ እንደምትፈልግ ለአዲሱ ጠ/ሚኒስትር መልዕክት የሚያስተላልፍ መሆኑን ድርጅቱ አስታውቋል።
በአሜሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ባደረጉት ግፊት ህጉ መጽደቁን የገለጸው ሂውማን ራይትስ ወች፣ ከዚህ ውጤት ተነስተው አሳሪ የሆነ ህግ እንደሚወጣ ስራዎችን እንደሚሰሩ ተስፋ እንደሚያደርግ ድርጅቱ ገልጿል።
ውሳኔው የተመድ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን በኢትዮጵያ ተገኝቶ ነጻ ምርመራ እንዲያካሂድ የሚጠይቅ የህግ አንቀጽ እንዳለው የገለጸው ሂውማን ራይትስ ወች፣ በአዲሱ ጠ/ሚኒስትር አማካኝነት ኢትዮጵያ እስካሁን የያዘቸውን አቋም ቀይራ በአገሪቱ የተፈጸሙት ግድያዎች በነጻ ወገን እንዲጣራ ህጉ እንደሚጠይቅ ጠቁሟል።