የአሜሪካ ኢምባሲ ወደ ኢትዮጵያ የሚሄዱ ዜጎች ጥንቃቄ እንዲያደርጉ አሳሰበ

ግንቦት ፳፭(ሃያ አምስት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ኢምባሲው ማስጠንቀቂያውን ያወጣው አልሸባብ በኢትዮጵያ  እና በምእራባዊያን ተቋማት ላይ ጥቃት ለመሰንዘር ፍላጎቱና ችሎታው እንዳለው ተጨባጭ መረጃ እንደደረሰው ከጠቀሰ በሁዋላ ነው።

በኢትዮጵያና በሶማሊያ ድንበር አካባቢ የሰዎች ምልልስ ተጠናክሮ መቀጠሉን የጠቀሰው ኢምባሲው፣ ጥቃቱ የሚፈጸምበት ቦታና ሰአት በትክክል ባይታወቅም፣ የአሜሪካ ዜጎች የምእራባዊያን ዜጎች በሚሰበሰቡበት በሆቴሎች፣ በምግብ ቤቶች፣ በመጠጥ ቤቶችና በገበያ አዳራሾችና በአምልኮ ቦታዎች ላይ ሁሉ የግል ደህንነታቸውን እንዲጠብቁ አሳስቧል።

አልሸባብ በኬንያ ላይ ተደጋጋሚ ጥቃቶችን ሲሰነዝር ቢቆይም በኢትዮጵያ ላይ እስካሁን ይህ ነው የሚባል ጥቃት ፈጽሞ አያውቅም።

የኢትዮጵያ ጦር ወደ ሶማሊያ ተመልሶ ከገባ በሁዋላ በአልሸባብ ላይ በሰነዘረው ጥቃት ድርጅቱ በርካታ ቦታዎችን ለቆ ለማፈግፈግ ተገዷል።

የኢትዮጵያ መንግስት በአሜሪካ ኤምባሲ መግለጫ ላይ የሰጠው አስተያየት የለም።